Friday, April 7, 2017

" መ ሿ ለ ኪ ያ "

#ሳteናw

… ሁሉም ለነብሱ ብቻ በሚሮጥባት፣ራስ ወዳድነት በተንሰራፋባት ሀገር፣ አንዱ አባል የችግር ቀዳዳ ከገጠመው ሌሎቹ ቀዳዳዋን ለመድፈን የሚያደርጉት  ሩጫ ትዕንግርት ይሆንብሃል። ከምቾታቸው ይልቅ ለአባላቸው ምቾት ቅድሚያ መስጠት የዘወትር ተግባራቸው ግርምትህን ያንረዋል። በመካከላቸው ያለው መተሳሰብ መተዛዘን፣ አንዳንቸው ለአንዳቸው መስዋዕት ለመከፈል ያላቸው ጥልቅ ሞራል ስትመለከት "አጂብ" ትላለህ   መሿለኪያዊያን ወጣቶች ከምን አይነት ማህበረሰብ በፍቅር ታንፀው እንዳደጉ፣ ለማወቅ ያጓጓሃል። አዎ!  ዛሬ የተላበስከው ስዕብና የትላንት አስተዳደግህ አሻራ ነው።

እንዚህም ወጣቶች ከማህበራሰባቸው የወረሱትን ይህን የፍቅር እሴት ጠብቀው ለማዝለቅ  በምርጥ ማዕከላቸው ሆናለች መሿለኪያ።

አንድ ቀን ሳተናው ከአንድ ልጅ ጋር በስራ እንቅስቃሴ አለመግባባት ተፈጥሮ ልጁን ይመታዋል። የተመታው ልጅ ብዙ ጓደኞች ያሉትና በፀብ ጊዜ እውነታውን ሳይረዱ እንደ አንበጣ ተሰባስበው የመተጋገዝ አባዜ ያለበባቸው ናቸው። ቢሆንም ሰው ይለያሉ። ከፀቡ ቡሃላ ፀጉረ ልውጥ ሰጎረምሶች መሿለኪያ  መጡ። ከመካከላቸው አንዱ  "ሳተናው ማን ነው?" ሲል ጠየቀ። በዚህ ጊዜ ቡፌት ቱር ብሎ ተነስቶ አቤት እኔ ነኝ ሲል ከፊታቸው ቆመ። እርግጥ ነው መሿለኪያዊያን ተባብሮ በመደባደብ ባያምኑም ተባብሮ ለመጣ አካል ግን የመልስ ምት ለመስጠት ወደ ኋላ አይሉም እንኳን ለአባላቸው፣ ለሌላውም ይተርፋሉ። ቡፌት ለሳተናው ሲል ከጎረምሶቹ መሀከል የጅምላ ዱላውን ለመቀበል ሰወጣ፣ ከውስጥ ሌላው አባል በተጠንቀቅ እየጠበቁ ነበር። ጎረምሶቹ እንደታሰቡት ሳይሆን፣ እቃ ወደ ክፍለ ሃገር በመኪና ሲጭኑ የዋሉና መኪና ሞልቶባቸው የተረፋቸውን እቃ መሿለኪያለማሳደር የመጡ ነበሩ። የቡፌት ሁኔታና ከውስጥ የፈጠጠባቸው አይን ብዛት  ግር ያላቸው ጎረምሶች። ለዘብ ባለ ድምፅ "አይ እቃ ተርፎን ለማሳደር ነበር? ሳተናውን አናግሩት ስለተባልን ለመጠየቅ ነው" አሉ። ሳተናው ትውልደ መርካቶና የመሿለኪያ አባል በመሆኑ እንደ ሌላው መጤ ተባብረው ሊያጠቁት አልደፈሩም። ዋናው ነጥብ ሳተናው እያለ ሳለ ቡፌት ለሳተናው ሲል ከጎረምሶቹ መሀከል የጅምላ ዱላውን ለመቀበል በመካከላቸው መገኘቱ፣ አንዳቸው ለአንዳቸው ምን ያህል ድረስ መስዋዕት እንደሚሆኑ ማሳየት ነው።

የፍቅር መማሪያ ሳትሆን መተግበሪያ፣ የመተሳሰብ ማደሪያ፣ የአንድነትን ጥቅም ምርጥ ማሳያ፣ መሿለኪያ። መሿለኪያ



   በወራሪው ጣሊያን በተመሰረተችውና በአፍሪካ ገላጣ ገበያነት ግንባር ቀደም በሆነችው መርካቶ ውስጥ…  ሁሉንም እንደ አቅሙ በማኖር የእናትነት ሚና ተጫዋች በሆነችው መርካቶ እንብርት ተመስርታለች። …  ኪስን ሳታይ እኔ ነኝ ያለውንም ቱጃር፣ ያጣ የነጣውንም  ጠብሻም በየደረጃው አብልታ አጠጥታ በምታሳድረው መርካቶ… ውስጥ… የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ መዲና አዲስ አበባ የኢኮኖሚ ሞተሯ በሆነችው መርካቶ ክልል … በመሀል አዲስ አበባ በ17 ካሬ የሰፈረች በመኖሪና በሱቆች የተጥለቀለቀች በሆነችው በእምዬ መርካቶ… ወጣት አባላቶቿን [መሿለኪያዎችን] በፍቅሯ፣ ሰብስባ፣ ውስጧ በሚሰፍነው፣ መረዳዳት ናፍቆት ጫሪ የሆነችው … መሿለኪያ።
 
… ከዳርና እስከ ዳር በተገጠገጡ ንግድ ቤቶች መሀል ድንገት የምትገኝ፣ ጣራና ግድግዳዋም ድፍን የሆነች ዋሻ፣ በመሆኗ ነው መሿለኪያ የሚለው ስያሜ በአባላቿ የፀደቀላት።

መሿለኪያ ወጣት የነብር ጣት ለሆኑ የመርካቶ ወጣቶች መሰብሰቢያ፣ ደስታም ሀዘናቸውን፣ ማሳለፊያ፣ ቢያገኙም ቢያጡም፣ መዋያ። መወያያ፣ መማማሪያና፣ መረዳጃ ማዕከላቸው ናት።

  መሿለኪያዎች በተለያየ፣ የእድሜ፣ የእምነት፣ የገቢና የትዳር ሁኔታ ላይ ይገኛሉ። በጠቅላላ ወንዶች ናቸው። ከመሿለኪያ ጋር በያዛቸው ፍቅር ሰበብ፣ በአዘቦት ቀናት ከስራ ቡሃላ፣ በእረፍት ቀናት፣ በበዓላት ቀናት ሳይቀር፣ ከዋሻዋ አይጠፉም፣ በዚሁ ሳቢያ ለማህበራዊ ህይወት የሚሆን ትርፍ ጊዜ ባይኖራቸውም፣  ከማህበራዊ ኑሮ የወጡም፣ ቢሆንም ቅሉ በመሿለኪያ የራሳቸውን ማህበረሰብ መስርተዋል።  በመሰረቷት መሿለኪያ ውስጥ ያለው ግንኙነት ለሌላው ህብረተሰብ አርዓያ መሆን የሚችል የኢትዮጲያዊነት ስሜት ያለውና በህረተሰቡ ውስጥ የሚታየው፣ የጠባብ ብሄርተኝነት፣ በለው የጎሳ ልዩነት፣ የሚባሉ ዝባዝንኬዎች በመሿለኪያ ጣሪያ ስር፣ ሞተው የተቀበሩ ናቸው። አንዱም ይህ ነው መሿለኪያዎችን ለየት የሚያደርጋቸው የአስተሳሰብ ልኬት። የመሿለኪያ ወጣቶች፣ እርስ በእርሳቸው፣ ያለ ልዩነት ይዋደዳሉ፣ይረዳዳሉ። ለመሰብሰቢያ ማዕከላቸው መሿለኪያም ልባዊ ፍቅር አላቸው።

በአጋጣሚ አንድ አባል አስገዳጅ ሁኔታ ገጥሞት ከመሿለኪያዋ ቢርቅ፣ በናፍቆቷ ሟች ነው። አስሬ እየደወለ በሀሳብ መሿለኪያ ለመሆን የሚያደርገው ጥረት የማይቀር ጉዳይ ነው።

ይህ ቁርኝት ያለ ነገር አልሆነም። ወጣቱ በመሻለኪያ ውስጥ ነፃነት አለው፣ ሀሳቡን ለአባላት የመግለፅና የማስተላለፍ፣ የራሱን ፍልስፍና የማካፈል፣ ታመነበትም አልታመነበት የመደመጥ እድል አለው።  በመካከላቸው ያለው የእርስ በእርስ መተሳሰብ፣ አንድ አባል ሲቸገር የሚደረገው መረዳዳት፣ በደስታውም በሀዘኑም ከጎኑ የመቆሙ ባህሉም ጭምርም ነው መሻለኪያን ተፈቃሪና፣ ተናፋቂ ያደረጋት። ይህ ብቻ አይደለም፣ የመሿለኪያዎች ባህሪይ በስራ እንቅስቃሴያቸው ከተለያዩ ስዕብናዎች ጋር የሚያገኙትን ልምድ፣ በትምህርት የተደገፉ፣ ብሎም ከመገናኛ ብዙሃን፣ ከመፅሃፍት፣ ከኢንተርኔት፣ የሚገኙ መረጃዎችና፣ እውቀቶች በሙሉ በመሿለኪያ ስብስባቸው አምጥተው የመወያየት ባህል በማዳበራቸው፣ መሿለኪያን፣ ሁሌ በተለያየ አጀንዳና ሁኔታ ስለሚያሳልፏት፣ የፍቅሯ እስረኛ አድርጓቸዋል። የእርስ በእርስ፣ መረዳዳት፣ መተዛዘን ለአንዱ ደስታ፣ ሌላው በደስታ መስዋዕት መክፈል፣ የመሿለኪያ ወግ ልማድ መሆኑ፣ የሰነባበተ ጉዳይ ነው።
ዛሬ በሀገራችን የተንሰራፉት የዘር፣ የሀይማኖት ወዘተ… ልዩነቶች መሿለኪያ ውስጥ አባልን ከአባል የሚለዩ ወሰኖች ሆነው በፍፁም አይገኙም። ለሀገር ለወገን ጠቃሚ የሆኑ ሀሳቦች፣ በተለያዩ ዘርፎች ልምድና እውቀት ባላቸው መሿለኪያዊያን ይብላላሉ፣ ወደ ተግባር ለመለወጥ፣ የሚችሉትን ያደርጋሉ።

   ሲጠቃለል መሿለኪያ በአራት ግድግዳ የተወሰነች ስፍራ ትሁን እንጂ፣ ለመሿለኪያዎች የሚሰበሰቡባት መሰብሰቢያ አዳራሻቸው ነች። መወያያ መመካከሪያ፣ ውሳኔ በድምፅ ብልጫ የሚያፀድቁባት ፓርላማቸው ነች። መብያ፣ መጠጫ፣ ቀልድና ቁምነገር መጨዋወቻ፣ መዝናኛ ስፍራ ነች። እርስ በእርስ የሚረዳዱባት የቴሌቶን መድረካቸው ነች። ወቅታዊ፣ አለም አቀፋዊ ሀገራዊ መረጃና ዜናዎች የሚለዋወጡባት፣ የሚሰሙባት፣ የሰሙት የሚያካፍሉባት መገናኛ ብዙሃናቸው ነች። መሿለኪያ ለመሿለኪያዎች ይህ ሁሉ ነገራቸው ነች ቢባል ግነት እንዳልሆነ በቀይ ብዕር ይሰመርበት። ታዲያ መሿለኪያዎች በእረፍት ቀን፣ በበአል ቀን ሳይቀር ሁሉም ነገር  በምትሆንላቸው መሿለኪያ ከማህበረሰቡ ሸሽተው መሰብሰቡ ሱስ ቢሆንባቸው፣ የሚገርምህ ነገር ነው?

ወገሬት!!

Wednesday, April 5, 2017

ለውጡ

"ለ     ው     ጡ"
#ሳteናw

  ግማሽ እፍኝ የሚሆነውን የላይ አባዲር ት/ቤት ትውስታዬን፣ በታች አባድሩ ፅሁፌ፣ እንደምቸከችከው ቃል የገባሁ ቢሆንም ቅሉ፣ ከጉዳዩ ኢ–አሳሳቢነትና ከነሻጣ ማነስና አንፃር ሳልፅፈው እስከዛሬ ዘግይቻለው። ዛሬ ግን በአንዲት የማህበራዊ ድረገፅ ወዳጄ አነሳሽበት፣ የቻልኩትን ያህል ልቸከችከው ነሸጥኩ።

    ከዜሮ ክፍል አስከ ስድስተኛ ክፍል ድረስ ብቻ ከሚያስተምረው ታች አባዲር ስድስተኛ ክፍልን በአንዳች ተዓምር አልፌ፣ በመቶ ሜትር(radius) ክልል ውስጥ ወደ ሚገኘው (ሌላኛው ቅርንጫፍ) ላይ አባድር ሰባተኛ ክፍል ስገባ ከታችኛው አባድር አንፃር ብዙ ለውጦች መታዘብ ቻልኩ። ልዩነቱ የጀመረው ገና ከአጥር በሩ ነበር። … ልሙጥ ቆርቆሮ በሞራሌ ስሪት የነበረው የታች አባድሩ ዋና በር፣ በላይኛው አባድር በዛሬ ዘመን ተጠፍጥፎ "ሁለት ሲኖትራክ ሊወጣው ይችላል" ብለህ ለመከራከር የሚያበቃህ ወፍራምና አጭር ብረት በር ሆኖ ተገኘ። ሲቀጥል ከበሩ አቅራቢያ ሁሌም ተሰይመው በሚገኙት ጥበቃዎች ጋሽ ሲራጅና ጋሽ ፀጋዬ(ስማቸውን ከተሳሳትኩ አርሙኝ) መካከል የነበረው ልዩነት ሆነ።  በተፈጥሮ ወጣ ወጣ ብለው በበቀሉ ጥርሳቸው ሳቢያ፣ ሁሌም የሚስቁ ከሚመስሉት ከታች አባድሩ ጥበቃ ጋሽ ስራጅ ሁሌም ከበሩ የሚቀበለን የፈገገ ገፅታ በተቃራኒ፣ ከነጭ ጎፈሬ ፂማቸው ጋር ቀይ በቀይ ቢለብሱ የገና አባት የሚመስሉትና እጅግ ሲሪየስ ገፅታ ባላቸው በላይ አባድሩ ጥበቃ ጋሽ ፀጋዬ፣ ሁሌም በማይፈታ ገፅታ  ተተካ። በት/ቤቱ በነበረኝ ቆይታ ጋሽ ፀጋዬ አይደለም ሲስቁ፣ ሲያወሩ እንኳ ጥርሳቸውን አይቼው አላውቅም ብል ግነት አይደለም። ምናልባት ጥርሳቸውን ገጥመው ያወሩ ይሆናል። ታዲያ ዛሬ ላይ ሆኜ የሁለቱ ጥበቃዎች ልዩነት ሳጤን!! አይ ተፈጥሮ እንደው ስታዳላ! ያስብለኛል። እዚህ ጋር ጥበቃው ጋሽ ፀጋዬ ከተማሪው ጋር የሚያገናኛቸው ተግባር ታወሰኝ። ዘወትር ትከሻቸው ላይ በማይታጣውና፣ እንደ አንዳች ነገር በሚጮኸው ጅራፋቸው፣… ወንጭፉን እያወናጨፈ ከማሽላው ማሳ ላይ እዋፋትን እንደሚያባር እረኛ፣ የአስቸጋሪ ተማሪዎችን ስብስብ በጅራፉ ጩኽት በማስደንበር የሚያባርሩትም ደርጊታቸው ከግማሽ አፍኝ ትውስታዬ ውስጥ የራሱን ድርሻ ይይዛል።

ሌላው ለውጥ ደውሎቹ ነበሩ።  በጋሽ ስራጅ አጋፋሪነት ብረትን ከብረት አጋጭቶ በሚፈጠር ድምፅ የነበረው የት/ቤቱ ደወል፣ እንደ ድሮ ስልክ ጢርርርር ወደሚል በኤሌክትሪክ ደወል ተለወጠ። ከባህላዊነት ወደ ዘመናዊነት የተደረገ ሽግግር! ብለህ ፈርጀው። ታዲያ መብራት ሲሄድ ደወል የሚበሰረው በጋሽ ፀጋዬ የጅራፍ ጩኸት ነበር !! ብዬ ብቀልድ ሀቅ እንዳይመስልህ Lol። እንደሻማ ነበልባል በትንሽ ትንፋሽ ይርገበገቡ የነበሩት የታችኛው አባድር  የመማሪያ ክፍል በሮች፣በድማሚት እንጂ በሌላ ሀይል የማይበገር በሚመስል በወፍራም የእንጨት በሮች ሆኖ በላይ አባድር አየው፣ በቀለም አልባ ቦሎኬት ግድግዳና ኢ_መስታወት በሆነ መስኮት የተማርኩበት የታች አባድሩ የነኮቱ የመማሪያ ክፍል፣ በድጋያማና ውስጣዊ ክፍላቸው በቀለም በደመቁ ክፍሎች፣ በከፊልም ቢሆን ባለመስታወት መስኮቶች ያሉት ሆኖ አገኘሁት። እንደ ወንፊት በተበሳሳው ቆርቆሮ ቀዳዳ ውስጥ ሾልከው ደብተሬ ላይ የሚለጠፉ ጨረሮች፣ (እጫወትባቸው ነበር)፣ እድሜ ኮርኒስ ለተባለ ቴክኖሎጂ በላይኛው አባድር አልነበሩም።  የሁለቱ አባድሮች የመማሪያ ዴስኮችም ቢሆኑ አራንባ ቆቦ ነበሩ። ገና ተማሪው ሲቀመጥባቸው፣ እያረገረጉና በሲቃ እያቃሰቱ ከረባሽ ተማሪዎች ይበልጥ፣ (የመምህር ፍራቻ ሳያግዳቸው) ክፍሉን ይረብሹ ከነበሩት ከታቹ አባድር፣ የተሻሉ ጠንካሮች ነበሩ። ምናልባት የት/ቤቱ አስተዳደር የተማሪው እድሜና ክብደት ላይ አባዲር ሲገባ እንደሚጨምር ስለተረዱ ይሆናል ይህን ሁሉ ለውጥ በላይ አባድሩ ያበጁት። በአጠቃላይ የታች አባድር ክፍሎችና የላይኛው ልዩነታቸው በሳሎን ቤትና በማዕድ ቤት እንዳለው አይነት ነበር። እናም ከአንደኛ እስከ ስድስተኛ ክፍል በኩሽና ብማርም ሰባትን በሳሎን ተማርኩ ብዬ ብዘባባት እንዳትፈርድብኝ።

ላይ አባዳር ከታች አባድሩ አንሶ የሚገኘው፣ በክፍሎች፣በመፀዳጃ ቤቶች ብዛት፣እና በቅጥር ግቢው ስፋት ነበረ። የላይ አባዲር ጊቢ ከጥበቱ የተነሳ፣ የአንድ ክፍል ተማሪዎች እንኳ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ለማሰራት የማይመች ነበት። በአካል ብቃት እንቅስቃሴው ሂደት፣ በመምህር መሀመድ ሱልጣን ፊሽካ እየተመራን እጃችን ስናጥፍ ስንዘረጋ፣ እጃችን በየክፍሎቹ መስኮት ይሾልኩ ነበር ብል እያጋነነኩ ቢሆንም፣ ከመጠን በላይ ጠባብ መሆኑ፣ያፈራቸው ተማሪዎች ምድክር ናቸው።

ለውጡ በት/ቤቶቹ ይዘት ብቻ አልነበረም። በትምህርት አይነቶችም ጭምር እንጂ።በመምህር ኤሊያስ የተማርኩት ኢትዮጲያዊው የሂሳብ ትምህርት፣ ዜግነቱን ቀይሮ "maths" ሆነ። በመምህር ኑር ሁሴን የተማሩኩት ሳይንስ፣ ባይሎጂ፣ ኬሚስትሪ፣ ፊዚክስ ተብሎ እንደ እንትን ሶስትም አንድም ሆኖ ተገኘ። ለሀገሬ የነበረኝ ፍቅር ወደር ስላልነበረው፣ ዜግነት የለወጡ ትምህርቶች ልክ እንደ ሶላቶና ባንዳ ስለምመለከታቸው፣ የተግባባንበት ጊዜ ትዝ አይለኝም። ለነገሩ የሚገባኝና በጣም ጥሩ የተሰኘ ነጥብ ማስመዘግብበት የትምህርት አይነት ቢኖር፣ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ተግባር ላይ ነበር።

… በአንድ የት/ ክፍል የስፖርት አስተማሪያችን የነበረው መሀመድ ሱልጣን፣ የመጀመሪያ የወር አበባ ማየቷ አስደንግጧት፣ ከቤቷ ኮብልላ ስለጠፋች ልጅ አገረድ፣ ትራጄዲ ታሪክ ሲተርክልን… እንዴ ከምኔው ከስፖርት አስተማሪነት፣ወደ ታሪክ አስተማሪነት ተከረባበተ ብዬ የተገረምኩበት… ገጠመኝ ሌላኛው ትውስታ ነው።

ጋሽ በቀለ በሚባል የጎማ አለንጋ፣ የእጃችን አንጓ እስኪናጋ ድረስ ይገርፈን የነበረው ኡስታዝ ፉዓድ በኛ ጊዜ፣ ዩኒት ሊደር ነበር(መሰለኝ)። ተማሪው ለሱ የነበረው ፍራቻ ከፍተኛ ነበር። የሱን መምጣት የምናውቀው፣ ጠብደሉን የቅጥር ጊቢውን ብረት በር፣ እያንገጫገጨ በሚንኳኳው ድምፅ ነበር። በዚህ ጊዜ በስድስቱም ክፍል ያለ ተማሪ፣ በመምህሩ ፍራቻ ሽንቱ ባያመልጠው ይመጣ ይመስለኝ ነበር።

ባይሎጁ መምህር ባልሳሳት ቲቸር ፀጋዬ፣ በአንድ የትምህርት ክፍለ ጊዜ፣ ስለ ሲጋራ መጥፎነት፣ ሲያተምሩን፣ በአባታዊ ምክር "አደራ ልጆቼ ሲጋራ፣ በምንም መልኩ እንዳትለምዱ"እያሉ በራሳቸው ህይወት ላይ የፈጠረውን ተፅዕኖ እንደምሳሌ እየገለፁ ብለው የመከሩን መቼም አይረሳኝም" ዛሬ በህይወት የሌሉት የእኚሁ መምህር ምክር (ነብስ ይማር)፣ አብረውን ከተማሩ ውስጥ አጫሾችን ሳይ፣ ምክራቸው በከፊል መምከኑን ታዝቤያለው። በላይ አባድር የነበረኝ ቆይታ የአንድ አመት ብቻ በመሆኑ ከዚህ በላይ ትውስታዬን ወደ ቃላት፣ ሀረግና ዓረፍተነገር (convert) ማድረግ አልቻልኩምና በዚሁ ልንካው።

ወገሬት!!