Friday, June 23, 2017

"ሰው > ይበልጣል"

" ሰ ው > ይ በ ል ጣ ል !"
# ሳteናw

"ገንዘብ ካለ በሰማይ መንገድ አለ" ልክ ነው። ገንዘብ ካልከፈልክ መች በአውሮኘላን መጓዝ ትችላለህ?  አይደለም መጓዝ። አየርመንገድ ገብተህ ሰው መሸኘትም መቀበልም አትችልም። ዘመኑ የገንዘብ ነው። ይህ ማንም ሊክደው የማችል ሀቅ ነው። ዛሬ ገንዘብ የማይገዛው ነገር የለም። ፍቅር ይገዛል፣ መልካም በማድረግ፣ የሰዎችን ቀልብ በፍቅር ትገዛለህ። "ዉይ! እሱ ቸር እኮ ነው!!" አስብሎ በሰዎች ልብ ቦታ ያሰጥሃል።
ዛሬ ሰው በብሩ፣ እንደ ጠቢቡ ሰለሞን ባለ ብዙ ሚስት ለመሆን በየቀኑ ሚስት መከራየት ተችሏል።

በገንዘብ ቁንጅናና መልክ ትገዛለህ። በእድሜ ብዛት የተሸበሸበ ቆዳ፣ እንደ ጎማ ታስለጥጣለህ። እድሜ ሰርጀሪ ለሚባል ህክምና። በገንዘብ፣ፆታ ይለወጣል። አዳሞች በብራቸው ሄዋን እየሆኑ ይገኛሉ። ሄዋንያን አዳምን ለመሆን፣ በጭኖቻቸው መሀል ጉጥ ያስተክላሉ። ባል የሌላቸው ባለሀብት ባልቴቶች፣ የወጣት ባል ዝርዝር፣ እንደ ምግብ አይነትበሜኑ ቀርቦላቸው፣ ጠቦቱን፣ ከሙክቱ፣ በላቱ በባቱ እንደበግ አማርጠው ቤታቸው ድረስ ያስመጣሉ። ላስተናገዳቸው ጠቀም ያለ ጉርሻ ይሸጉጣሉ። ወዳጄ በዚህ ዘመን ገንዘብ ከማያደርገው የሚያደርገው ይልቃል። ሀቀኛውን ውሸታም ያሰኛል። ውሸታሙን፣ የእውነት አባት ያስብላል። ዘፋኞች፣
"እያለህ ካልሆነ፣ ከሌለህ የለህም!" በሚል በተወራረሱት ዜማ
የደሃን ሞራል እንክትክቱ አውጥተዋል። ፈጣሪ ይይላቸው!!በቁምህ ሞተሃል ሲሉ ተሳልቀውበታል። የገንዘብ ሰባኪያን እንደ ፈጣሪ " ሁሉን ቻይ ኤልሻዳይ፣ምን ይሳንሃል!"  ምናምን እያሉ አምልከውታል። በውዳሴ ዘምረውለታል።

ዛሬ ላይ የገንዘብ ነገር እዚህ ደረጃ የደረሰ ቢሆንም ቅሉ፣ የገንዘብ አቅም የማይበግራቸው በርካታ ጉዳዮች አሉ። ሊያደርጋቸው የማይችሉ ነገሮች የሉም አላልኩም! ወላ አልወጣኝም። እርግጥ ነው ህመምና፣ መድሃኒት ይግዛ እንጂ፣ ጤና አይገዛም። ባልም! ሚስትም! ይግዛ እንጂ በዲኤንኤ ቁርኝት ያለው የአብራክ ክፋይ ልጅ አይገዛም። ልብ በል! ህይወት ያጣፍጣል እንጂ ህይወት አይሆንም።የሰው ዘር በሌለበት፣ ብቻህን ትሪልዮነር ብትሆን፣ እመነኝ ራስክን ታጠፋለህ እንጂ፣ በህይወት ለሶስት ቀን አትዘልቅም። ገንዘብ ስጋን እንጂ መንፈስ አይሸምትም። ቁስ እንጂ ደስታ አያስገኝም። ቅንጡ ቪላ ይገንባ እንጂ፣ የህሊና ምቾት አያስገኝም። ለንብረትህ ኢንሹራንስ ትገባበታለህ እንጂ፣ የወደቀበትን አደጋ አትታደግበትም። ነገርን ነገር ያነሳዋልም አይደል እሚባል። ይህን እውነታ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ገጠመኝ ልንገርህ። 

… ጊዜው ውድቅት ሌሊት ነው፣ ቦታውም የንግድ ቤቶች ከዳር እስከዳር ተገጥግጠው ባሉበት መርካቶ። ባለሀብት ተብዬ ፣ አገር አማን ብሎ ሱቁን  ቆልፎ፣ ሄዷል። ቆልፎ መሄድ ብቻ ሳይሆን በገንዘቡ የቀጠራቸው ዘቦቹን አስጠብቋል። ድንገተኛ እሳት ከአንዱ ሱቅ ይነሳል። ዘብ ተብዬው እንቅልፉን ዧ ብሎ ተኝቷል። ይህን እሳት ማን ያያል በአቅራቢያው ያለ በረንዳ አዳሪ ወንድሞች። ተጯጩሆ ና ተረባርቦ፣ እሳት የተነሳበትን ሱቅ በር ገንጥለው።  እሳቱን ያጠፉታል። በዚህ የመጣ በግራና በቀኝ የነበሩ ብዙ ሱቆች፣ የእሳት እራት ከመሆን ይተርፋሉ። ልብ በሉ! ሱቆቹ ቢወድሙ ቢድኑ የሚጠቀመው የሚጎዳው ባለ ሀብቱ እንጂ፣ እነዚህ ሰዎች አይደሉም። እንቅልፍ አጥተው ያዳኑት ንብረት ለጌታው እንጂ ለነሱ ምንም እንዳልሆነ እያወቁ ነው። ለባለ ንብረቱ፣ ከገንዘቡ ቀድመው የደረሱ እኚሁ ከሌላችሁ የላችሁም የተባሉ ምስኪን ወንድሞች ናቸው። የመርኬው ባለ ሱቅ፣ ከአደጋው የታደገው ገንዘቡ ሳይሆን ሰው ነው። ምነው "ከሌለህ የለህም" ያሉ ሁሉ! ኖረው ይህን ባዩ! እርግጠኛ ነኝ "ባይኖርህም፣ ትኖራለህ፣ ቢኖርህም፣ ትሞታለህ" በሚለው ቀይረው ነጠላ ዜማ ይለቁ ነበር። ያም ሆነ ይህ የሚቀድመውገንዘብ ሳይሆን ሰው ነው። የነገርኩህ አጋጣሚው ለዚህ ምርጥ ማሳያ ነው። በመሆኑም ከሰው ገንዘብን ያስቀደምክ ወንድሜ ሆይ! ስማኝ!! ያመለከው ሀብት የዘመርክለት ንዋይ፣ በእሳት ጠፍቶ እንዳያጠፋህ፣ ደርሶ እሳቱን ያጠፋልህ፣ሰው ነው። በድሎት ዘመንህ፣ በረንዳ ሲያድር  ዞረህ ያላየከው፣ ወንድምህ ነው። ለዛውም
ከሌለው የለም ስትል የተዘባበትክበት ወንድምህ። ባይኖረውም ኖሮ! ንብረትህን ካለመኖር አደጋ ተረባርቦ እንዲኖር፣ አድርጎ አኑሮ ያሳየህ!
ስማኝ ወንድሜ!! በሀብት ሰበብ የመጣ የስኳርና የደም ግፊት በሽታ በማትታወቅበት ስፍራ ድንገት ጥሎ ጣር ቢያንፈራግጥህ፣ ቀድሞ የሚደርስልህ፣ ሳይፀየፍ አፋፍሶ የሚያነሳህ፣ ሰው እንጂ ገንዘብህ አለመሆኑን እወቅ። አቅም ሲከዳህ፣ የሚደግፍህ ሰው እንጂ ብር አንዳይደለ ተረዳ። ብትሞት፣ ቀድሞ ደርሶ የአሞራ ሲሳይ ከመሆን ታድጎ፣  በወጉ ከፍኖ የሚቀብርህ ሰው ነው። የትራፊክ ህግ ለራስህ ደህንነት ስትል፣ ቅድሚያ ለእግረኛ ስጥ! ይልኻል። እኔም እልሃለው ለራስህ ስትል ቅድሚያ ለሰው ስጥ።
ወገሬት!!

Tuesday, June 20, 2017

" እ ወ ዳ ታ ለ ው "

" እ ወ ዳ ታ ለ ው "
#ሳteናw

… አቤት ስወዳት!! እንደሷ የምወደው ሴት ምድር ላይ አለ እንዴ? እኔንጃ ያለ አይመስለኝም!! በጣም ውድድድድ በቃ!! እስኪገርምህ ድረስ። ብወድሽ ብወድሽ አለሰለችህ አለኝ! ሲል ቴዲ ለፍቅረኛው ቢዘፍንም እኔ ግን ይህን ዘፈን የምዘፍነው ማህፀን ለምትጋራኝ እህቴ ነው። ይገርምሃል!! ነብሱን ይማረውና አባቴ በስነ ተዋልዶ ዙሪያ ታታሪ ተራቢ ነበርና ብዙ እህቶች አሉኝ። የእህት ሀብታም ነኝ። እንደሷ ልወዳቸው ብሞክር እንኳ አልተሳካልኝም። መውደድን ስለፈለከው ሳይሆን፣ የውስጥ ስሜትህ የሚሰጥህ መሆኑን እዚህች ጋር በቀይ እስክሪብቶ አስምርበት። እስክሪፕቶ አልያዝክም? በቃ የሃሳብ መስመር አስምርበት። ልትወደው ብትሞክር እንኳ የማይሳካልህ ነገር ገጥሞህ አያውቅም? ሌሎቹ እህቶቼ በህፃንነቴ ቢንከባከቡኝ፣ ሀቢቢ፣ገልቢ፣ ሩሂ፣ ምናምን እያሉ ከመካከለኛው ምስራቅ በተዋሱት  ቋንቋ ቢያቆላምጡኝ!! በሰቅሉኝ፣ቢክቡኝ፣ ቢቆልሉኝ ወላ ሃንቲ!! እሷግን እየተጣላንም፣ እየኮረኮመችኝም፣እየሰደበችኝም ከጓደኞቿ ጋር ስታወራ "ምንድነው?" ብዬ አፌን ከፍቼ ልሰማ ፈልጌ፣ ሂድ ውጣ ሴታ ሴት ብላ፣ ነጠላ ጫማ ወርውራ ብታባርረኝም! እወዳታለው። ወረኛ እንድሆንባት አትፈልግማ!!

አቤት!! የውዴታዬ ብዛት! ስህተተኛ ብትሆን እንኳ ለሷ ወግኜ ከእህቶቼ ጋር ተጣልቻለው። ለምን ቅር አሰኟቿት ስል ለረጅም ግዜ አኩርፌያቸዋለው። ስህተቷን የሚጋርድብኝ ኢፍትሃዊ ሆኜ አይደለም። ወይም ከሷ የተለየ ነገር ስለምጠቀም አይደለም። በቃ ለረጅም ግዜ ከሌሎቹ በተለየ አብሮ ማደጋችን የቸረኝ ፍቅር። የሚገርመው የፍቅር ልውውጣችን ለሁለታችን እንጂ ለማንም አያስታውቅም። አጠገብ ላጠገብ፣ ስንከራከር ስንጨቃጨቅ ብታየን። "ድንቄም መዋደድ ብለ ልታሽሟጥጥ ትችላለህ" (ያው ማሽሟጠጥ ስራህም አይደል!!)። አይገባህማ!! ፍቅራችን ለራሳችን እንጂ ላንተ አይታይህማ። እንዲታይህ የኔን አይን ተከራይተህ እሷን፣ አልያም የሷን ማያ ተውሰህ እኔን ማየት አለብህ።  የዛኔ ትረዳዋለህ።

  የዝንጀሮ ባል፣ ሲላፋት ሲያጫውታት፣ አይተህ አቤት ፍቅራቸው ሮሚዮና ጁሊየት ምናምን ትል ይሆናል።  እውነት አይምሰልህ። አንድ ቀበሮ ቢመጣ ፈሱን እያንጣጣ ነው ጥሏት የሚነካው። ኮስተር ጀንተል ብሎ ከሚስቱ አጠገብ የተቀመጠ አንበሳ አይተህ ደግሞ "ምን እንደባላባት ይጀነናል!" ትልም ይሆናል  አንድ አደጋ ቢከሰት ቀድሞ ይሞታታል እንጂ፣ እንደ ዝንጀሮው ጥሏት አይነካውም። አየህ የተግባር ፍቅር ይሉሃል ምሳሌው ይሄ ነው። ለሰው የማይታይ በልብ ያለ ፍቅር!! በለው። የኛንም ፍቅር በዚህ መስለው። "ካላየው አላምንም ብለህ ከገተርክ ተወው"። ነገር ግን ሳያዩ ያመኑ ብፁአን ናቸው። የሚለውን የመፅሀፍ ቅዱስ አንቀፅ አስታውስሃለው። እኔ ለሷ የማልሆነው ነገር ቢኖርም፣ እሷ ለኔ ማትሆነው የለም!! ለኔ ካሏት ህይወቷን እስከመስጠት ትደርሳለች። ይሄን ዝም ብዬ የምተረተረው ሳይሆን በተደጋጋሚ በእውነታ ያረጋገጥኩት ሀቅ ነው። ነገርን ነገር ያነሳዋል አይደልም እሚባል። ከነሱም ውስጥ አንዱን ገጠመኝ ልንገርህ።

…  ከአስር አመት የአረብ አገር ቆይታ ብኋላ ይሕቺው ውዷ እህቴ ለአገሯ በቃች። በዚህም ደስታችን ወደር አጣ። በሀሴት ሰከርን። በዛው ሰሞን የቀድሞ ህይወቷ በገጠር የነበረውን እናታችንን ለመጠየቅ፣ በሷ እስፖንሰርነት ወደ አገርቤት፣ ሁለት ዘመዶቻችንን አስከትለን ሄድን።

በአገር ቤት የነበረን ቆይታ ከትውስታ የማይጠፋ አስደሳች ነበር። እንደቱሪስት ተዝናናን።በመጨረሻም መዝናናታችን፣ ሮንግ ተርን እንደሚለው ፊልም ጫካ ለጫካ በጨለማ በመረራሯጥ ተፈፀመ እንጂ። በገጠር የነበረን አስደሳች ቆይታ፣ የመጨረሻው ምሽት ተከታዩ ነበር።
በምሽቱ በእናታችን ጎጆ ቤት ውስጥ የነበረው ድባብ ደማቅ ነበር። ወዳጅ ዘመድ በቤቱ ተኮልኩሏል። ከምድጃው አጠገብ ባለው ቋሚ ምድጃ ላይ የሚነደው ፍልጥ ከሙቀት አልፎ የቤቱ ብርሃን ሆኗል። እስከዛሬ ድረስ ቃናው የማይረሳኝን የቡና ቁርስ ቆጮ በአይብ በልተን አብቅተናል። ጨዋታው ደርቷል። በአንድ በኩል እናቴ ቡናዋን እንደያዘች ከጎረቤት ሴቶች ጋር ወግ ይዛለች።  እኔ ከታላቅ እህቴ እግር ላይ ተንተርሼ፣በጀርባዬ ተኝቼ፣ ፀጎሬንእንደማከክ ስትደባበሰኝ፣ በልጅነቴ የአያቴን ድርጊት አስታውሶኝ በሃሳብ ነጉጃለው። እሷ አብረውን ገጠር ከሄዱት የወንድሜ ሚስትና፣ የታላቅ እህታችን የባል ወንድም ጋር የጋራ ወይይት ይዘዋል። ከጎጆ ቤቷ ክበብ የሩብ ጨረቃ ቅርፅ ባለው በአንዱ ጥግ ላይ ባለው በረት ውስጥ ያሉ ከብቶች፣ በየመሃሉ ድምፃቸውን ሲያጓሩ፣ የገጠር ህይወን ከማጉሏታቸው ባሻገር፣ በቤቱ ድባብ የተደሰቱ ይመስላሉ። ከበረታቸው በላይ ያለው የማገዶ እንጨት ማከማቻ ቆጥ ነገር ላይ ባለው የዶሮ ቅርጫት ውስጥ ያሉ ዶሮዎች እንደ አላርም ሰዓት እየጠበቁ ይጮሃሉ። በሌላ ጥግ የታላቅ ወንድማችን ልጆች " በየመሃሉ የእናታቸውን እናንተ ልጆች አድቡ" የሚለውን ግሳፄ ከመጤፍ ሳይቆጥሩ ይላፋሉ፣ይስቃሉ፣ ይጣላሉ፣ ያለቅሳሉ። መልስው ይጫወታሉ።(አይ የልጅ ነገር።  ሁሉም በየራሱ ሙድ ፍንትው ብሏል።






ታላቅ ወንድሜ(ጉዳዩ) ብቻ ከበሩ አጠገብ ባለ በርጩማ ወንበር ላይ ገፅታውን አኮስሶ ተቀምጧል። ይህ ሁኔታው አላማረኝም። ይህን ሀሳቤን ለእህቴ በሹክሹክታ አካፈልኳት። "እሷም፣ ስጋቴ ገብቷት ኖሮ ህመሙ ሊነሳ ሲል እንዲህ ያደርገዋል" ብላ የማውቀውን የበሽታ አጀማመሩን አስታወሰችኝና። ወደ ጨዋታዋ ተመለሰች። አንድ የአጎቴ ልጅ ሰላምታ አስቀድማ ገባችና፣ ከነ እናቴ ስብስብ ተቀላቀለች።

ይህ መልካም ምሽት በንደዚህ ሁኔታ አልፎ ፣ግማሹ ወዳጅ ዘመድ ጠብጠብ፣ ደህና እደሩ እያለ ቀስ በቀስ ጭር ማለት ጀመረ።

ጉዳዩ ከተቀመጠበት በርጩማ ድንገት ፍንጥር ብሎ ተነሳና እንደጦጣ እየተንጠላጠለ፣ ከበረቱ በላይ ካለው እንጨት ማከማቻ ወጥቶ አንዳች እቃ እያተረማመሰ ይፈልግ ጀመር። በቤቱ ያለነው በሙሉ ትኩረታችን እሱ ላይ ሆኖ፣ በመድረክ ላይ ሰርከስ እንደሚያይ ተመልካች እናየዋለን።

ፍልጦቹን አተራምሶ አተራምሶ፣ የፈለገውን ነገር ሲያጣ፣ አንድ ትልቅ ፍልጥ አንደ ቀስት ወርዋሪ ፍልጡን ይዞ ቆመ። ሁኔታውን ስናይ ወደኛ ለመወርወር የተዘጋጀ ይመስላል።
"ተነሽ አንቺ ብሎ" ምቾቴ ሆና በተተንተራስኳት እህቴ ላይ ጮኸ። ጉዳዩ ከኔ ጋር መሆኑን ነጋሪ አላሻኝም። ብድግ ብዬ ቆምኩና "ወርደህ አነጋግረኝ?" ብዬ መፎከር ጀመርኩ።።ሁሉም ካለበት በድንጋጤ ቆሞ ይለምነው ገባ። ፍልጡን ወደኔ ለመወርወር ኢላማውን ለማስገባት ወደኔ አቅጣጫ አንድ ሁለት አያለ እንደመወርወር አደረገና በሶስተኛው ፍልጡን ወረወረው፣ በዚሁ ቅፅበት እህቴ ለተወረወረብኝ ፍልጥ እንደጋሻ በራሷ ልትመክት መጥታ ተለጠፈችብኝ። በትልልቅ አይኖቿ በሚሰረስር አስተያየት አፍጥጣበታለች። እንደሌሎቹ ሳትጮህ ሳትንጫጫ ጋሻዬ ሆናለች። የተግባር ፍቅር ተመልከት።

የተወረወረው ፍልጥ ማናችንንም ሳያገኝ ተመዘግዝጎ እግራችን ስር ወደቀ። እኔ እህቴን ከራሴ ለማላቀቅ እየታገልኩ እጮኻለው "ወንድ ከሆንክ ወረድና አናግረኝ" እሱ ሌላ ፍልጥ አነሳ ኢላማውን አስተካክሎ ድጋሚ  ወረወረ። የጎጆ ቤቱ ምሰሶ ጨርፎ አቅጣጫውን አስቶት በሚነደው ምድጃ ላይ ወደቀ። የእሳትና የአመድ ብና ጎጆዋን የዘመን መለወጫ ርችት የተተኮሰባት ሰማይ በጭስ፣ አመድና የእሳት ፍንጣሪ! ተሞልታ፣ በጨለማ ተዋጠች። ማንም ከማንም መተያየት አልቻለም ጫጫታና ጩኸት ብቻ።

እህቴን እንዳቀፍኩ የሆነ ሰው እጄን ይዞ እንድከተለው ጎተተኝ። እሷን ይዤ የሚገትተኝን እጅ ተከትለን ከቤቱ ወጥተን መሮጥ ጀመርን። ውጪውም እልም ያለ ጨረቃ የሌለበት ጨለማ ነበር። ወዴት እንደምንሄድ ሳናውቅ እየጎተተኝ የሚሮጠውን እጅ፣ እየተከተልን፣ በባዶ እግር መሄድ ያለመደው እግራችን እንደልብ እንዳንሮጥ ቢያግደንም፣ ጭቃው ቢያዳልጠንም፣ በማይታየው ጨለማ ሮጥን። መሪያችን እንዴት ታይቶት እንደሚመራን አላውቅም። አይኔ ጨለማውን እየለመደ እየለመደ መጥቶ በመጠኑም ቢሆን ይታየኝ ጀመር። የግቢ አጥራችንን ለቀን በአውራ ጎዳናው ቁልቁል ወረድን። የምትመራን ሴት ትሁን እንጂ ማን ትሁን ወዴት ትወሰደን የማውቀው ነገር አልነበረም። ወደ አንፍ ጎጆ አጥሩን አልፈን ወደ በሩ ተጠጋን። መሪያችን በሩን አንኳኳች። ""ማነው?" መሪያችን "እኔ ነኝ" ስትል በድምፇ አወኳት። የአጎቴ ልጅ ነበረች። በሩ ተከፈተ። ውጪ ከነበረው ጭለማ አንፃር፣ ጎጆ ውስጥ የምትንጨላጨለው ብርሃን በቂ ነበረች።  የከፈተችውም የአጎታችን ልጅ መሆኑን አወኩ። በድንጋጤ ክው ብላ ደርቃ ቀረች። ከሁኔታችን አንዳች ነገር ሸሽተን እንደመጣን ታውቋታል። መርታ ያደረሰችን የአጎቴ ልጅ በሩን ከውስጥ ቀርቅራ፣ ወደ መቀመጫው እያመላከተችን፣ የተከተለን ሰው ይኑር አይኑር በሩ ተለጥፈፋ አጣራችና መጥታ ከጎኔ ተቀመጠች። "ተረፋቹ? ፍልጡ አገኘኛቹ እንዴ?" አለችኝ። እህቴ ድንጋጤ አልለቀቃትም እንደተለጠፈችብኝ እየተንቀጠቀጠች ታለቅሳለች። "አይ አልነካንም" አልኳት። በድንጋጤ ደርቃ ቀርታ የነበረችው የአጎቴ ልጅ ፣ መሪያችን የሆነውን ሁሉ ስትነግራት። ድንጋጤዋ በረታ። "አዎ ቀን ሀያት(የወንድሜን ሚስት ማለቷ ነው) ሲነሳበት የሚይዘውን ጦር ከቆጥ አውርዳ፣ ስትደብቅ፣ አይቻት። ምን ሆነሽ ነው? ስላት። "ዛሬ ሁኔታው አላማረኝም" ብላኝ ነበር። እንደገመተችው ተነሳበት ማለት ነው?" አለች። አንዳች ነገር ከእግር እስከጥፍሬ አንጨረጨረኝ። አላገኘውም እንጂ ሊወረውርብኝ ሲፈልግ የነበረው ጦር ነበር ማለት ነው? ። ንዴት ይሁን ድንጋጤ ወረረኝ። "እሺ እንግዶቹን አዛው ጥዬ ነው የመጣሁት ይዣቸው ልምጣ አልኩ። የአጎቶቼ ልጆች አልፈቀዱልኝም። ቢፈቅዱልኝም በትክክል በጨለማው መሄድ መቻሌ እ ራጠራለው። "እኔ ሄጄ አመጣቸዋለው! ብላ መሪያችን በሩን ከውስጥ እንድትቀረቅር ለሌላኛው የአጎቴ ልጅ ነግራት ወጥታ ሄደች። እኔም እህቴም የሆነው ነገር ሁሉ እውነት እውነት አልመስል ብሎናል። ከአፍታ የነበርንበት ጎጆ በር ተንኳኳ። ድምፃችን አጠፋን።ልጅቷ ወደ በሩ ተጠግታ በማንሾካሾክ "ማን ነው አለች። መሪያችን ነበረች። እንግዶቹን ይዛ መጣች። እነሱም ድንጋጤ አርበትብቷቸዋል። ለአገሩ እንግዳ፣ ለሰው ባዳ በመሆናቸው ድንጋጤያቸው ከኛ ቢበዛ እንጂ አያንስም ነበር። ቀስ በቀስ ተረጋጋን። እኔቴና በቤቱ የነበሩ ሁሉ ጓዛችንን እንደያዙ ያለንበት ጎጆ መጡ። ተረፋችሁ ብለው ከጠየቁን ቡሃላ።  እኛ ከቤት ከወጣን ቡሃላ ስለተፈጠረው ነገር ነገሩን። ወንድሜ ይህን ከፈፀመ ቡሃላ የተፈጠረውን ነገር ማወቅ አልቻለም። ነብሱ በደንብ ከተመለሰች ቡሃላ እኛን"የት ሄደው ነው? " ብሎ  መጠየቁን። እራቱን በልቶ ጭልጥ ያለ እንቅልፍ እንደወሰደው ነገሩን። ያደረገውን ነገር አለማወቁ፣ በሱ እንዳንፈርድ አደረገን። ወደ አይደለም አልን።  እናቴ ግን ነገውኑ ወደ ከተማ እንድንመለስ አስጠነቀቀችን። ምን እንደሚፈጠር አይታወቅም ለማንኛውም እናንተ ሂዱ። እኛ እንደሚሆን እናደርጋለን ብላን። አስደሳቹን ጊዜ በአሳዛኝ ሁኔታ አጠናቀን፣ በማግስቱ ጉዞ ወደ አዲስ አበባ። ይህን ሁሉ ልዘበዝብልህ፣ የቻልኩት ለኔ ካሏት መስዋዕት ትከፍላለች ባልኩህ እህቴ ሰበብም አደል። አዎ!! ዛሬም ነገም! እወዳታለው!!

ወገሬት!!

Monday, June 19, 2017

" I N T E R V I E W "


#ሳteናw

   ሀገሪቱ የእህል እጥረት በገጠማት በአንድ ወቅት፣ ሊቀመንበሩ፣ የችግሩን ስረ መሰረት ለማወቅና ቀጣይ የመፍትሄ እርምጃ ለመውሰድ በሚል ከእህል ጋር ግንኙነት አላቸው ያሏቸውን አካላት ራሳቸው በቢሯቸው አስጠርተው ማነጋገር ጀመሩ! አሉ። አሉ ነው!! ምንም የተረጋገጠ ነገር የለም። አሉባልታ። በዚህም መሰረት ሶስት የዶሮ እርባታ ድርጅት ባለቤቶች ለኢንተሪቢ(interview) ከቢሯቸው በሰዓታቸው ተገኙ።

ሊቀመንበሩም፣ ከጀርባቸው፣ በሶሻሊዝም ርዕዮተ አለም፣ አርአያ የሚሏቸውን ሰዎች ፎቶ፣ በትልልቁ ከተሰቀለበት ቢሯቸው፣ በወታደራዊ አለባበሳቸው ፏ! ብለው! ተሰይመዋል።

ዶሮ አርቢዎቹ… በአጃቢ እየተመሩ ከቢሯቸው ገብተው ሲቆሙ፣ሊቀመንበሩ በአንድ እጃቸው የስልኩን እጀታ ይዘው እያወሩ ነበር፣ በግማሽ ልብ ሆነው በሌላኛው እጃቸው ለባለጉዳይ በተዘጋጀው ወንበር ላይ እንዲቀመጡ አመለከቷቸውና፣ ሰዎቹ ተቀመጡ። የስልክ ንግግራቸውን እንደጨረሱ፣ ከነበራቸው የጊዜ ጥበት አንፃር ቀጥታ ወደ ጥያቄያቸው ገቡ…

ለመጀመሪያው አርብቶ አደር… ወደሚቀርባቸው ወንበር እንዲቀመጥ አዘው።

"እሺ!!ለምታረባቸው ዶሮዎችህ መብልነት፣ የምታቀርብላቸው ጥሬ ምንድነው?" ሲሉ ጠየቁት የቢሮ ወንበራቸው ላይ እየተደላደሉና፣ መለዯቸውን እያስተካከከሉ።
"ስንዴ! ሲል በኩራት መለሰ። ወታደራዊ ማዕረግ!! ይሸልሙኛል በሚል።

"ምን!" አሉ ሊቀመንበሩ በድንጋጤ። "ስንዴ?! ክው ብለዋል!።

"ስንዴዴዴ?! እንዴዴ…ዴዴ!። ህዝቡ የሚበላው የለው አንተ ለዶሮ ስንዴ?" ለኢትዮጲያ አንድነት፣ ደሙን እያፈሰሰ፣አጥንቱን እየከሰከሰ ላለ ሰራዊታችን ለምናቀርበውን በሶ የስንዴ እጥረት ገጥሞን! አንተ ለዶሮችህ ስንዴ?! ነው እንዴ?" አሉ ብግን እንዳሉ።

"ና ማነህ?" ከአጃቢዎቻቸው አንዱን ጠሩ። አጃቢው መጣ።

"ይህን፣አናርኪስት፣የእናት ጡት ነካሽ፣ወስደህ የእጁን ስጠው።" ትዕዛዛቸው ውስጥ ከፍተኛ ቁጣ አለ። ትዕዛዙን የተቀበለው አጃቢ ወታደር፣ በወታደራዊ ሰላምታ ወለሉን በከስክሱ "ጓ" አድርጎ መሬቱን ሲደቃ፣ ቢሮዋ ተርገበገበች።
ሊቀመንበሩ ሳያስቡት ስለነበር አስደንግጧቸዋል።
"ምንድነው እንደዚህ አገር የሚያውክ ሰላምታ መስጠት?" አሉ በውስጣቸው በሰጠው ሠላም አደፍራሽ ሠላምታ እንደተሸበሩ።  አጃቢ ሆዬ! ገለል ወዳለ ስፍራ ወስዶ! ዷ …ዷ …ዷ… ድ… ው ሰጠውና … በፈጣን እርምጃ ተመልሶ ከቢሯቸው ከች። ሊቀመንበሩ የተቀበሉት በግልምጫ ነበር…

"ምንድነው ለአንድ ሰው ይሄ ሁሉ ሁካታ? እኔ በስንት ኡኡታና!ለቀሶ! በስንት ጩኽትና ልመና! አይደለም እንዴ የማመጣው? ጥይቱን! አይደለም ወይ? ትንሽ አታስብም? ሀገሪቱ የኔ ብቻ ነች እንዴ?" አሉት አሁንም እንደተቆጡ።

"በአንድ ድምፅ እርምጃውን ልውሰድ? ሲል በትህትና ጠየቀ አጃቢው።
"ለምን በአንድ? ከቻልክ በሰደፍ ገላግለው።"
አሉትና አቀርቅረው ማስታወሻቸው ላይ መፃፍ ጀመሩ። ቀጣዩ አርብቶ አደር በቢሮው ስፋት ተደንቆ ሲመለከት ሊቀመንበሩ ከአጃቢው ጋር የተለዋወጡትን አልሰማም ነበር። ይፅፉት ከነበረ ማስታወሻ ቀና እያሉ። እሺ አንተ! ብለው   ጥያቄውን ደገሙለት።

"የኔ ዶሮች የፈረንጅ ዝርያ ስለሆኑ፣ ስንዴ እንኳ ሊበሉ! ጫጩቶቻቸው እንኳ እንደ ብይ አይጫወቱበትም። ስለዚህ… ብሎ አፉን ለመጠራረግ ንግግሩን ገታ አደረገ።

ሊቀመንበሩ ምን ሊል ነው? በሚል ግርምት አፍ! አፉን! ያዩታል።
ቀጠለ … ስለዚህ … ዶሮዎቹ የአገራቸውን የአመጋገብ ስርዓት፣ ጠብቀንላቸው እንዲመገቡ ማድረግ፣እንግዳ ተቀባይ ኢትዮጲያዊነታችን ያስገድደናልና። ለነዚህ ቅንጡ ዶሮዎች የምንቀልባቸው፣ በትውልድ  አገራቸው እንደሚመገቡ በቅቤ የተለወሰ በቆሎ ነው። ለዚህም ነው የኛ ድርጅት የሚያረባቸው ዶሮዎች! ከየትኛውም የዶሮ አርቢ ድርጅቶች በተለየ፣ ባለ ሁለት ፈረሰኛ ሆነው መገኘታቸው። አለ…  በመመፃደቅ አይነት

ሊቁ፣ በመልሱ ቆሽታቸው አሯል። "በቅቤ የተለወሰ በቆሎ? ህም!! አሉ በምፀት።…አሁን አንተ የዶሮ አርቢ? ወይስ የዶሮ አራስ ተንከባካቢ? የምትባለው።… ከህዝብ ጎሮሮ ነጥቀህ! እያደለብካቸው ለምን? አራት ደንደስ አይኑራቸው? ህእ! ጉድ ነው! ደግሞ ስንዴ አይበሉም! በቆሎ፣ፈረሰኛ ምናምን ይለኛል እንዴ? ትሻልን ሰድጄ ትብስን አመጣው" አሉ።  ብስጭት! እብድ! ቅጥል! አሉ። ምርር አላቸው። ይህን ወንበር የወረሱበትን ቀን ረገሙ። "ቆይ! እኛ ከስንቱ ነው የምንዋጋው?"
አጃቢውን ጠሩ። አጃቢው ተጣሩ እቴጌን በሆዱ እየዘፈነ። ከች አለ። "ይህንንም የማይረባ አድሃሪ! የነጭ ቁስ አምላኪ! ከቻልክ ምናምኑን በመቀስ፣ ከልሆነ ቂጡን በሳንጃ በልልኝ።" አሉ። አጃቢው ትዕዛዙን እንደተቀበለ፣ ወታደራዊ ሰላምታውን ሊደግም… ባለበት ቀጥ ብሎ እንደቆመ፣ አንድ እግሩን ሽቅብ ወደላይ… ሰቅሎ… ሰቅሎ… ሰቅሎ…ጉልበቱ ደረቱ ጋር ሲደርስ፣ ለአፍታ አየር ላይ አቆመና፣ ወደታች ቁልቁል አንደርድሮ መሬቱን ሊደቃው ሲል…
"ቆይ …ቆይ… ቆይ … እያሉ ፍንጥር ብለው ከተቀመጡበት ወንበር ተነሱ። እግሩ መሬት ከመድረሷ በፊት ሊያስቆሙት። አጃቢው አየር ላይ የቀረ እግሩን እንዳንጠለጠለና፣ በቆመበት እግሩ ሚዛኑን ለመጠበቅ፣ እየታገለ "ምንድነው?" በሚል ተመለከታቸው።

"ነገርኩህ! ነገርኩህ! ይሄ ግንድ 
እግርህን፣ ድምፅ ሳታሰማ እንደሰቀልክ፣ድምስ ሳታሰማ አውርድ!አሉት። አይናቸውን እንዳፈጠጡበትና በትረ መኮንናቸው በማስጠንቀቂያ መልክ እየቀሰሩበትበት።

አጃቢ ሆዬ! አየር ላይ ተንጠልጥሎ ከቁጥጥሩ ውጪ የሆነበት እግሩን ጥርሱን ነክሶ፣ትንፋሹን ውጦ፣ ሚዛኑን አጥቶ እየተንገዳገደ ቀስ አድርጎ ድምፅ ሳያሰማ መሬት አስነካት፣ ሰውየውን ይዞ መውጣት ጀመረ

"ይሄን ጉልበት በባዶ ሜዳ ከምታመክኑት፣ ልማት ላይ ብታውሉት ምን አለ? " እያሉ ወደ መቀመጫቸው ተመለሱ።

ተግሳፃቸው ከኋላው እየተከተለው። ኮቴውን ሳያሰማ በጥፍሩ እየተራመደ ሄደ። በሰውየው ገለል ካለ ስፍራ ወስዶ እርምጃውን ሲወስድበት ምንም አይነት የተኩስ ድምፅ፣ ሳያሰማ፣ተመልሶ ከቢሮው ገባ። ያለምንም ተኩስ እንደሸኘው የታዘቡት ሊቀመንበር
"በሰደፍ ነው?" አሉት።
"አይ "
"እና… "
"ለሰላምታ አውጥቼው የነበረው ጉልበት መክኖ እንዳይቀር፣ ጓሮ ወስጄ በጀርባው ካስተኛሁት ቡሃላ፣እዚህ እግሬን አንጠልጥዬ ካቆሙኩት፣ ጀመርኩና፣ በከፍተኛ ሀይል ቁልቁል አንደርድሬ፣ልቡ ላይ በማሳረፍ፣ሸኘሁት።"

"በጣም ጥሩ! በጣም ጥሩ!። እንዲህ ንቁና ፈጣን ወታደር ነው የሚያስፈልገን፣ ብለው አመስግነው። ወደ መጨረሻው ዶሮ አርቢ ዞረው ። "እሺ አንተስ?" ሲሉ ጠየቁት ስልችት መንፈስ… ይሄኛው ነቄ ነው። አቻዎቹ ገለል ወዳለ ስፍራ ተወስደው፣ የደስታ ርችት እንዳልተተኮሰላቸው ወይም በድምፅ አልባ ጭብጨባ እንዳላመሰገኗቸው አውቋል። ስለዚህ አንድ ዘዴ ፈጥሮ ማምለጥ አለበት። በመጨረሻም ይህን መልስ ሰጠ "ጌታዬ! እኔ እንኳን፣ ስንዴም፣ በቆሎም አልቀልባቸውም። ገንዘቡን ነው አንድ ሁለት ብዬ ቆጥሬ የምሰጣቸው።ገንዘቡን ወስደው ምን እንደሚበሉት ግን እኔንጃ።" ሲል መለሰአሉ። ልብ አርግ አሉ ነው!! ምንም የተረጋገጠ ነገር የለም። አሉባልታ።
ወገሬት!!

Friday, June 16, 2017

" ግ መ ሌ ን ም አ ስ ራ ለ ው… "


#ሳteናw

ሁሌም በተለመደው፣ ጊዜ፣ ቦታና ሰዓት፣ ሁሉም መሿለኪያውያን ከአፍጥር ቡሃላ በመሿለኪያዋ ተሰብስበዋል። ቀን በፆም እንደ ቁርበት ደርቆ የዋለ ሁሉ፣ አሁን ዘና ብሏል። ይጫወታል፣ ይሳሳቃል፣ ይጯጯሃል፣ ይቅማል። አዲሱ የፉአድ መንዙማ "ሰላም ነጃ" እያለ ከብሉቱዝ እስፒከሩ ይሰማል። በጉርዷ በርሜል እሳት ይነዳል! በእሳቷ ዙሪያ ተቀምጠዋል። ትኩስ ነገር የሚሸጡ ልጅ አገረዶች፣ የቡናና ሻይ፣ በማቅረብ ረገድ ገበያቸውን አጧጡፈውታል። የጥንቱ የመርካቶ የረመዳን ምሽት ድባብ፣ ጨርሶ እንዳይጠፋ ይመስል፣ በመሿለኪያ ብቻ ይታያል። በምርቃና ሚናነት የነበረው ጫጫታ ቀስ በቀስ ወደ ፀጥታ ሲለወጥ፣ ሁሌም ፀጥታ ጠብቆ መወያያ ድንገት ርዕስ በመክፈት የመታወቀው ሰያ ነጭ ሽንኩርት ዛሬም በድንገት ፀሎትም ምኞትም የመሰለ ንግግር ያንበለብል ጀመረ…

"… ያረቢ በዚህ ረመዳን ይሁንብህ … የተረጋጋች ህይወት፣ መሽታ በነጋች ቁጥር አዳዲስ የምትሆን ቀን። አለ አይደል አሁን እንዳለው አንድ አይነት ከሆነ አዋዋል ተቃራኒ የሆነች። ደግሞ… ተረጋግታ ምታረጋጋኝ፣ የህይወቴ አጋር። ቀን በተረጋጋ ውሎዬ… ናፍቄ፣ ማታ እስካገኛት የሚጨንቀኝ ሚስት። ገና ስገባ ከበሩ… "ሀቢቢ!እንኳን ደህና መጣህ!"ብላ ከንፈሬን በከንፈሯ ጨብጣ ምትቀበለኝ። ቀን ያበሳጨኝን ጉዳዮች ሁሉ፣ ልብ በሚያጠፋ አሳሳሟ የምታጠፋልኝ። አጠገቧ ስሆን፣ ደስታ የተባለ ሁሉ፣ እንደ ዛር በላዬ ላይ ሰፍሮ፣ የሚያንዘረዝረኝ። መቼም የተራዘመው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኢሳት ማየት እንጂ ምኞት አይከለክል። በመሆኑም እመኛለው!! አርቄ አልማለው። ደሃ በህልሙ ምናምን ብለህ ደግሞ ሙድ ጋማ!።በል አሉህ። ምድረ በርሜል!!። እኔ ከምሬ ነው። የሚያሳካው እሱ ነው። ይሄኔ እኮ በዚህም ያሳከከህ አለህ!! የራስህ ጉዳይ! ብቻ የተረጋጋች…

"አረ!! ቆይ … አረ!! ቆይ… እስኪ ተረጋጋ! አበድክ እኮ!! " ሳተናው እየጮኸ አቋረጠው።

"ይኸው!! ምን አልኩ? ምን ብዬ ነበር? አያችሁ ሲያሳክከው! እንዳንተ አይነት ምቀኛ እያለ በየት በኩል እንመኝ? ስማ አከክም አላከክም፣እኔ እመኛለው። ተረጋግቼ አልማለው። ተስፋ እስንቃለው። ፀሎት ጠዋት ማታ አደርሳለው። በአስተማማኝ ሁኔታ መሰረት ያለው የተረጋጋና በቂ የገቢ ምንጭ ያለው መተዳደሪያ፣ የተግበሰበሰ ብር ባልጠላም የተግበሰበሰ ኑሮ  አልፈልግም! በቃ የተረጋጋ! ብቻ የምፈልገውን ማድረግ ያስችለኝ!!ከዛ ውጪ ወላ ሃንቲ!! ከሚስቴ ጋር ተረጋግተን ……

"አረ ባክህ ተረጋጋ አንተ ሰው!! "ቡፌት ነበር ያቋረጠው። "ምንድነው ብቻህን ምታብደው!? ግልፅ አድርገውና አብረን እንበድ?! 

"ዝም በል! እኔ አላበድኩም ምኞቴን ነው የለመንኩት!!"

"ድንበሩን ያለፈ ምኞት ከእብድ ነው !! ስለዚህ እመነኝ ሰያ አብደሃል፣ ደግሞም እብድ ሁሉ አብጃለው አይልም እኮ! እንደፈረደብን ይህን ልጅ የሆነ መላ ተፈላልጠን  አማኑኤል ሆስፒታል እናስገባው እንጂ!! ዝም ትላላችሁ እንዴ? ጎበዝ? "

"አረ! የአማኑኤል ጂኒ ይፈለጥህ! አን ግባሶ! ሟርተኛ፣ ደግሞ መመኘትም ልትከለክለኝ ነው?" በሰያ ቀልዳዊ ስድብ መሿለኪያን አስገምጋሚ፣ የሳቅ  ወጀብ አናወጣት።

"አይደለማ!ሰ…" ብሎ ጀመረ ሳተናው። "…ስትመኝ ካለህበት ነባራዊ ሁኔታ አንፃር ሊሆን ይገባል!! ለትልቁ ምኞትህ ቢያንስ ቀድመህ ሁለት እርምጃ መቅረብ አለብህ። ሰው ሚልየነር ሆኖ ቢልየነርነት ቢመኝ አግባብ ነው!! ለቂጡ ጨርቅ የሌለው ትሪልዮነር ያርገኝ ቢል ይሄ ሰው በእርግጥ አብዷል። አንተም ሳስብህ ልክ እንደዚህኛው ሰውዬ እያበድክ ነው … ቅድሚያ የምትመኘውን እወቅ። ሚስት ከመመኘትህ በፊት፣ ራስህን ማስተዳደር መቻልህን አረጋግጥ። ከቤተሰብ ጥገኝነት ተላቀህ ያለማንም ድጋፍና እርዳታ በመቆም ሀላፍትናን ልትለማመድ ይገባል። ይህን ስታረጋግጥ ሃላፍትናዎችን መሸከም እንደማይከብድህ ስታምን፣ ትዳር ምናምን የተባሉ ነገሮችን በርህን ክፍት አድርገህ ትመኛለህ፣ ብሎም ትፀልያለህ።፣ የዛኔ ተግባርህ፣ ከፀሎትህ ጋር ተጋግዞ ወለል ካለው በርህ ይገባልሃል። ይህ ነው አካሄዱ። ዝም ብሎ ተቀምጦ ድንበር የጣሰ ምኞት እብደት እንጂ ሌላ አይደለም።" ሲል ሳተናው ሁሉም በጥሞና  ያደምጠው ነበር።

"የምኞት ድንበር ቸካይ ያደረገህ ማን ነው ባክህ? ደግሞ የሚያሳካው ፈጣሪ ነው" አለው ሰያ በአንድ በኩል የሳተናው ንግግር እውነታነት እየታየው።

"ልክ ነው! አለው የንግግሩን ቅላፄ ወደ ቁም ነገር እየለወጠ። "እንዳልከው የሚያሳካው ፈጣሪ ነው! እኔም ሳጥናኤል ነው አልወጣኝም። ዋናው ነጥቤ ግን ፈጣሪ የሚያሳካልህ፣ አንተ መንቀሳቀስ ስትጀምር፣ ነው። ለስኬትህ መጀመሪያ፣ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ጀምር ነው። ይሄን ሳታደርግ እጅ እግርህን አጣጥፈህ፣ፈጣሪ ነው የሚመግበኝ ብለህ፣ በርህን ዘግተህ ብትውል፣ ጠኔ ይቀረጥፍሃል እንጂ፣ በአረቢያንስ ናይት ተረት ተረት መፅሀፍ ላይ … እንዳለው ታሪክ፣ አላዲን ፋኖሱን ሲፈትግ እንደሚመጣው ጂኒ፣ ጣፋጭ ምግብ፣ በወርቅ ሳህን አሳብዶ አያቀርብልህም። ገብቶሃል? የምልህ?።  ለመብላት፣ መንቀሳቀስ መስራት ይጠበቅብሃል፣ የዛኔ ፈጣሪም እገዛውን ያደርግልሃል። ስራህን ያገራልሃል፣ ይመግብሃል። የራስህ ጥረትና ጥንቃቄ ሳታደርግ ፈጣሪ አዳኝ ነው፣ ጠባቂ ነው፣ብለህ ብቻ ከምትደረድርበት ኤፍኤስአር ላይ ተወርወር እስኪ? በፓራሹት የሚቀልብህ መሰለህ? የሚያድንህ፣ የሚጠብቅህ፣ መጀመሪያ፣ መጠንቀቅ ስትችል ነው። እራስህን ስትጠብቅ ነው። ግልፅ ነው? ብሎ ቀና አየው ሳተናው።

  የንግግሩ እውነታነት ፍንትው ብሎ የታየው ሰያ ነጭ ሽንኩርት! አሁን ተረጋግቶ በአዎንታ ራሱን ነቀነቀ። ማላገጥ ሟንጓጠጡ ቀርቶ፣ ሁሉም በቁም ነገር እያደመጡ መሆኑ ሲረዳ ሁሉንም የሚያማክል ወቅታዊ ሀሳቡን አከለ…" ባይሆን ሁላችንም ከተግባር ለውጥ ጋር ያለንበት የረመዳን የመጨረሻው አስር ቀን ፈጣሪ የባሮቹን ፀሎት ከየትኛውም ግዜ በበለጠ የሚቀበልበት ጊዜ ነው። ልንጠቀምበት ተገቢ ነው። ይሄ ለሊቱን ሙሉ መቃማችን ቀርቶ በተሃጁድ ሰላት ላይ፣ እንለምነው። ደግሞ ተሃጁድ ሰላት ላይ፣ ይሄን ገለምሶ አፍሰን አፍሰን፣ ለቅሶአችን ከፋቲሃ ጀምሮ፣ የሰጋጁን ጥሞና የሚሰርቅ እንዳይሆን እንጠንቀቅ። ልብ አድርጉ!! አናልቅስ አላልኩም!!ማልቀስ ካለብን በስርዓት ድምፅን ቀንሰን፣ ሌላውን ሳናውክ አልቅሰን እንማፀነው። የተግባር ለውጣችንንም ከዚህ ጊዜ ጀመሮ፣ እንተግብረው… የሚናገረው ከልቡ ነበር። "…ቆይ! ለውጥ አንፈልግም? ለውጥ አትፈልግም ጄጃን? ለውጥ አትፈልግም ቡፌት? አንተስ ጃንደረባው ለውጥ አትፈልግም? ቅድም ሰያ የተመኘውን በህይወታችን እንዲፈፀም ሁላችን አንሻም? እርግጠኛ ነኝ የሁላችንም መልስ "እንፈልጋለን" ነው። ስለዚህ ተግባራዊ እንቅስቃሴ እንጀምር።  አረቦች እንደሚሉት "ግመላችንንም እንሰረው፣ በአላህም እንመካለው"። ምን ለማለት ነው? ከፀሎታችን ጎን ለጎን ለፍላጎታችን መሳካት የተግባር እንቅስቃሴ ወሳኝ ነው ። እንደውም ዛሬውኑ፣ እላፊ ወጪ ለመቀነስና ለመቆጠብ፣ ፈጣሪም ይረዳን ዘንድ የተሃጁድ ሰላት ብንጀምርስ?። ልክ አይደል እንዴ? ሲል ሁሉንም ጠየቀ። "አዎ"ሲሉ ከልባቸው በህብረት መለሱለት። አላህም ያግዛቸው።
ወገሬት!!

" አ ታ ሳ ዝ ን ም … ወ ይ ?"


====================
#ሳteናw

… በስሙ የምጠራው ወንድ አያቴ ድንኳን በሚያክል ካቦርቱ ወሽቆኝ፣ የወፍቾ ኳስ ሲሰራልኝ ጭላንጭል ትውስታዬን የቀረፅኩባት ስቱዲዬ ነበረች። ፍቅሩን ሳላጣጥም፣ ትውስታው በህሊናዬ ግብዓቱን በደንብ ሳያከማች፣ የቤቱ አንደኛው ምሰሶ ወንድ አያቴ ከሰማይ ቤት ተጠርቶ ሲለየን፣ በእዬዬ የለቅሶ ቀጠና ሆና የተሸኘባት ቤቴ። በብረት ምጣድ፣ ሚናነት ከሳሎን ወደ ሻወር ለውጠናት ገላችንን ታጥበን በእቅፏ የተጠቀለልንባት ፉል ውሃችን።ወይ እሷ ምን ያልሆንባት አለ? አረ ምንም!!

በመጀመሪያ … Granዶቼ የፍቅር ምሰሶ ሆነው ገነቧት፣ የጋተ የናቴን ጡት ያለጊዜው ትቼ፣ የሴቷ አያቴን ደረቅ ጡት እየጠባሁባሁ አደኩባት። እስከ ጉርምስናዬ መጀመሪያ ድረስ ህይወቴ መልህቋን ጥላ የረጋችባት ወደብ፣ ታሪኬን የመዘገብኩባት ድርሳን፣ ሀዘን ደስታዬን የተወንኩባት መድረክ!! ነበረች ቤቴ። ገራዤ በህክምና ይሁን በግብርና መሳሪያ እንደገረዘኝ እንጃለቱ፣ ትንሿ ቆለጤን ሲከረትፍ፣ በፈጠረው ስህተት፣ ፊኛዬ ደህና ቡጢ እንቀመሰ መንጋጭላ አብጣ፣ በዚሁ ሰበብ የሽንት ቧንቧዬ ጠባ፣ ለሶስት ቀን መሽናት ቢያቅተኝ፣አያቴ ጭንቀቷ አላስቆም አላስቀምጥ ብሏት፣ ቢጨንቃት ቢጠባት፣ ዱዓ ለማስደረግ ቆጮና አይብ ተደግሶባት፣(የዚን ሁኔታ መሉውን ማንበብ ከፈለክ የዳዶቃዋ በሚለው ርዕስ ታገኘዋለህ!) በወደጅ ዘመድ እናቶች ዱዓ ለቆለጤ ተለምኖባት፣ በዚሁ ሰበብ ልትፈነዳ የደረሰችው ፊኛዬ፣የፀሎታቸው ጥሪ በፈጣሪ ፈጣን ምላሽ አግኝቶ፣ በመካከላቸው ተበልቅጬ በጀርባዬ እንደተኛው ሽንቴ ወደ ኮርኒሱ ተንፎልፎሎ የተነፈስኩባት፣ የአያቴና የእናቶች ደስታ በእልልታ የደመቀባት፣ ከሷ አልፎ በመርካቶ ያስተጋባባት ነበረች። ይህቺው የዛሬ አሳዛኝ…ቤቴ። ቀይ ፖፖዬን በጳውሎስ ኞኞ ትንግርት መፅሄት ሰበብ፣ የተውኩባት እናት ሀገሬ ነበረች… በአያቴ ልጆች፣ በምላቸው እህቶቼ! ወንድሞቼ። የስጋ ወላጆቼን ከነመፈጠራቸው ሳላስተውል በፍቅር ተከበብቤ ያሳለፍኩባት ዋሻዬ።  ለመጀመሪያ ጊዜ የህፃናት መዋያ ተመዝግቤ፣ ትምህርት የተጀመረ ቀን ስሄድ በአቅሚቲ ዝንጥ ዝንጥንጥ ብዬባት። አሁንም አሁንም ያለ ማቋረጥ፣ እንደ ግሉኮስለሚንጠባጠበው ንፍጤ መቆጣጠሪያ መሃረብ፣ የኮት ደረቴ ላይ በመርፌ ቁልፍ  አንጠልጥዬ፣ እንደ ዘማች በስቄና ትጥቄ ታጅቤ፣ የወጣሁባት፣
በግንቦት 20 ማግስት…
"ደርግ ያሳደገው ሌባ፣
ኢህአዴግ ይቀጣዋል" እያልን ምንነቱ በውል ያልተገለፀልልን፣ ቤት ማይመታ ግጥም፣ እንደ መዝሙር ከአቻ ጓደኞቼ ጋር በህብረት የዘመርንባት፣ የኪነት ክበባችን።

  ደግሞ በዛው ሰሞንበሰፈሬ መርካቶ  ጩሉሌ የወርቅ፣ ይሁን የነሃስ ሰዓቱ የተቀማው የደርግ ወታደር" ሌባውን ውለዱ ሲል"በከባድ መሳሪያው፣ የአናቷን ክፈፍ ድብድቦ ወንፊት ያስመሰላት(የወርቅ ሰዓት ቢሆን እንጂ፣ ለነሃስ ሰዓትማ ይህ ሁሉ ጥይት ያባክናል አልልም)። ሳምታዊዉ የአያቴ የቡና ስርዓት ሲፈፀም፣ የእጣን፣ የአይብና ቆጮ ጠረን ያወዳት፣ በጭሳጭሷ ሳቢያ ሁሌም ሚያድፈው ላንቃዋን(ኮርኒሷን)፣ የረመዳን ፆም በመጣ ቁጥር በቀለም ቀቢ ያስቀባናት፣ አልያም እንደ ቀለም ቀቢ በበርሜልና መሰላል ላይ ተንጠላጥለን ከእህቴ ጋር፣ ኦሞ በራሰ ብጣሽ ጨርቅ የወለወልናት፣ ውሃ እየተረጫጨን ተሳስቀን የፈነደቅንባት የዘመናችን ኤድናሞል የህፃናት መዝናኛ አለም። ከጓደኞቼ በጨዋታ ተጣልተን ተማትቼ ና፣ ሸሽቼ የተደበኩባት ምሽጌ። ሁሌም ግሳፄዋ በኩርኩም የሚጀምር በሆነው፣ ትልቋ እህቴ ኩርኩም በለቅሶ ያላዘንኩባት። ቴቪ ሲገባባት እንደ ሀገር መሪ፣ ደማቅ አቀባበል ያደረግንባት መስክ። አቤት የዛን ለት ቲቪ ብርቅ ሆኖብን፣ ለቲቪው ደህንነት ሲባል በታላላቅ ወንድሞቼ የተቆለፈባት፣ መሽቶ ቲቪ ስናይ ባልጠፋ ቦታ ለአራት አንድ አልጋ ላይ በፍቅር ሰፍቶን የተኛንባት። ወይ አሳዛኝቷ። ቤተሰቡን ብሎ የመጣ ዘመድ፣ ወዳጅ  ያስተናገድንባት፣ እንደራሱ ቤት በነፃነት ያሳለፈባት። ካሏት ክበብ በሶስተኛው፣ በጊዜው ጎረምሳ የነበሩት የታላላቅ ወንድሞቼ ባልንጀሮች ተመሽገው እንደ ፊደል ሀ… ሁ… እያሉ በታላቆቼ የኔታነት የሱስ አይነት ቆጥረው የተማሩባት። እየኮረኮሙ የሚሹትን(የፈረደብኝ እኔን) የላኩባት። በጅምላ ያፈቀሯትን የጎረቤት ቆንጆ፣ ደብዳቤ ያለመታከት የተላላኩባት። (ምናለ ለአንዱ እንኳ እሺ ብትል እስኪ?!)። የቱጃር ቤት ወግ ደርሷት መደበኛ ስልክ የገባባት ዕለት፣ ከት/ቤት ስመለስ፣ አያቴ ሰላት ላይ ብትሆንም፣ ዜናውን እስክትነግረኝ አላስችል ብሏት፣ በጣቷ ጠቁማኝ፣ ስልኩን ወፍራም ትራስ ላይ ተቀምጦ፣ እንደ አመት በዓል ድፎ! ዳንቴል ለብሶ ሳየው በአግራሞት የጮህኩባት፣ቤቴ። ሚስኪን ስታሳዝን።  አመታዊ በዓላት ኢድና አረፋ፣ በመጡ ቁጥር ከትውስታ በማይጠፋ መልኩ በደማቁ ያከበርንባት። ለኢድ የተገዛልኝን ልብስና ጫማ እስኪነጋ አላስችል ብሎኝ ለብሼ የተኛሁባት ድንክ አልጋዬ!!። ለአረፋ በዓል ምክኒያትነት የተገዛውን በሬ ከጓደኞቼ ጋር፣ የኛ ይበልጣል የኛ ይበልጣል ስንል፣ የተፎካከርንባት። የዛን ሰሞን ቁርስ፣ ምሳ እራት፣ ክትፎ በቅቤ፣ የጠጣንባት። በመጨረሻም (ፎላ) ሻኛው ድፍኑን ተቀቅሎ ወዳጅ ዘመድ፣ በተገኘበት በባህላዊ የቡና ስነ ስርዓት፣ በአያቴ እንደ ተቆራጭ ኬክ ተቆራርጦ ና ታድሎን በልተን፣ በሬውን ከብልቱ፣ እስከ ጥፍሩ ደረስ፣ አንድም ሳናስተርፍ ቁርጥምጥም አድርገን በልተን፣ መጨረሳችንን ያወጅንባት። እህቴ ለማንም የማይቀረው ጉዞ ወደ አረቡ አለም በሄደችበት ምሽት፣ እኔና አያቴ መኝታዋ ባዶ ሲኖንብን፣ ገና በአንድ ቀኗ ናፍቆቷን መቋቋም ተስኖን፣ በውድቅት ሌሊት፣ ከእንቅልፍ ባነን ተቃቅፈን ያነባንባት። አቤት አንድነታችን፣ አቤት ፍቅራችን!! ይህን ሁሉ ነገር በእቅፏ ሸሽጋ ያስተወነችን መድረክ!። ታላላቅ ወንድም እህቶቼን ተኩለው ሲዳሩ፣ ፣ጉሮ ወሸባዬ ፈንጥዘን የሰረግንባት። አልቅሰን፣ ሙሾ አውርደን ሬሳ በየተራው የሸኘንባት ነበረች። ደግፋ ይዛት የነበረችው አንድ ምሰሶ(አያቴ) በሞት ተጠልፋ ስትድቅ፣ ፍፁም ተቀየረች የማናውቃት የማታወቀን ሀገር ሆና አረፈች። የታሪክ ድርሳንነቷ ቀርቶ፣ የታሪክ አተላ ሆነች!! በሳቃችን እንዳልሳቀች፣በዳንሳችን እንዳልተውረገረገች፣በለቅሷችን እንዳላነባች፣የሆነውን እንዳልሆነች፣የጠላነውን፣ እንዳልጠላች፣ የወደደነውን፣ እንዳልወደደች። ቤተሰቡን ያለ አንዳች አድሎ በፍቅር አስተሳስራ እንዳላኖረች ሁሉ። ዛሬ ግን ክፉ ቀን መጣና፣ የጋራው ፍቅር በራስ ወዳድነት ተለወጠና። የአንድነት ፍቅር ጠፋና፣ ከሰው ገንዘብ አስበለጠችና እሷም በአቅሟ  እንደዘመኑ ሰው ፍትሃዊነቷ የውሃ ሽታ ሆነና፣ ለባለጊዜ አንድ ወገን አደላችና፣ "ገንዘብ ካለ በሰማይ መንገድ አለ" ሲሉ ሰምታ ራሷን ሰማይ ሰቀለች። ገንዘብ ተከትላ ሄደች። ታች ያለ ቤተሰቧን በተነች፣ አይኗን በጨው አጥባ አላውቃችሁም ስትል ካደች። ካደመው አደመች፣ትላንት የኔ ነበረች ብሎ ሚዘክራት፣ ዛሬ በሰማይ ላይ ያለች፣ ወተቷን የማያይ የታሪክ ላም ሆነች። ሁሉም አዘነባት!! ይብላኝላት ለሷ እንጂ!! እኛማ ጊዜ ሳይለውጠን አለን። ከምር ግን! አታሳዝንም ወይ? …
ወገሬት!!