Saturday, April 30, 2016

ጃ ያስተሰሪያል!

  ጃ ያስተሰሪያል… ጃ ያስተሰሪያል… የሚለውን የቴዲ ዜማ የወጣው  በጉርምስናዬ መጀመሪያ አካባቢ ነበር። ዜማው በፖለቲካ ውጥረቱ ሰሞን ብርቅ ሆኖብኝ አስሬ እየደጋገምኩ እቤት በሶፋ ወንበር ላይ እንዳህያ እየተንከባለልኩ በስሜት አይኔን ጨፍኜ ተመስጬ አብሬ አዜማለው። ሲዲውን ያቅሙ ወሰን ድረስ በለቀጥኩት… ሙዚቃ እንኳን ለራሴ ለመንደሬ በቂ ነበር። ይህ ተደጋጋሚ ደርጊቴ ያበሳጨው ታላቅ ወንድሜ … በአካባቢው አለመኖሩ ጠቅሞኛል … (ወንድሜ ሲቆጣ በቀልድ እያዋዛ ሲሆን በሚቆጣበት ጊዜ የሚያሳየው ድምፅና እንቅስቀሴ አለመሳቅ ያልፈለገን ሁሉ በግድ ያስቃል) ካሁን አሁን መጣብኝ እያልኩ ዘፈኑን አብሬ አዜማለው ከዜማው ከያንዳንንዱ ስንኝ ጋር የራሴን ስዕላዊ ምናብ አየፈጠርኩ በስሜት ማድመጤ ቀጥያለው… ስፒከሩ ይጮሃል…እኔም ከስፒከሩ በላይ ድምፄን ለማጉላት ፎቴው ላይ እየተንደባለልኩ እዘፍናለው አይገልፀውም… እሰነጠቃለው…!

ግርማዊነታቸው ከዚህ ሰረገላ
ወደ ዋገን ወርደው ሲተኩ በሌላ
በዛውንቶች ራስ ስድሳ ጉድጓድ ምሳ
አብዮት ሞላችው የተማሪ ሬሳ

ዘንድሮ ፈርቻለው በተማሪ ሬሳ ታሪክ ተረኛው እኛ እንዳንሆን ብቻ። ሰግቻለው!! ቢሆንም ዜማውን አብሬ አዜማለው… ግጥሙን ከምኔው በቃሌ እንደያዝኩት ለራሴም ገርሞኛል። ምናል እንደዚህ ትምህርት ቢያዝልኝ? ሰባተኛ ክፍል ፈተናው በዜማ ቢሆን ኖሮ እንኳን ሶስቴ ልወድቅ ከሴክሽን አንደኛ ነበር ምነቀንቀው። ለምን የትምህርቱ አሰጣጥ በዘፈን መልክ አይኮንልንምግን? ኪኪኪ አስበው እስኪ ቲቸር ታመነ ፊዚክስ እየዘፈነ ቢያስተምረን? በራሴ ሃሳብ በጣም ሳኩ። የስምንተኛ ክፍል ፊዚክስ አስተማሪዬ ታመነ ምን አይነቱ ባለ ውቃቤ ወይ ደብተራ መተቱን እንደደገመበት አይገባኝም። ያለ ስራ መቀመጥ የማይችል ፍጡር ቢኖር ቲቸር ታመነ ነው። ሌላው ቲቸር ታመነን በተሰተካከለ አለባበስ ማየት ዘበት ነው። ወይ ኮሌታው ተዛንፏል ወይ የጫማ ክሩ ተፈቶ እያንዘላዘለ ወይ ያለካልሲ ጫማ ተጫምቶ ማየት የተለመደ ነው። እረፍት ቡሃላ የሚያስተምረው ክላስ ካለው የደውሉ ማብሪያ መጥፊያ ካለበት ስፍራ ዳስተሩን ቾኩንም ማስተማሪያ መፅሀፉንም አቅፎ አስሬ ሰአቱን እያየ ለመደወልና ለማስተማር የሚቁነጠነጥ አስተማሪ ነበር።ይህ ድርጊቱ እንኳን ለኛ ለተማሪዎች ለሌሎች አስተማሪዎችም ሳቅ የሚያጭር ባህሪው ነበር። ከዚህ ባህሪው ጋር እየዘፈነ ሲያስተምረን በአይነ ህሊናዬ ሳየው ነበር ሳቄን መቋቋም ያቃተኝ። ትኩረቴን… ወደ ዜማው ተመለስኩ…

ጃ ያስተሰሪያል… ጃያስተሰሪያል…

<<አንተ እብድ አረ ቀንሰው>> አለችኝ ፈቲያ የወንድሜ ባለበቤት።

<<ፈቱ የመጨረሻ ነው ይኼ ብቻ ይለቅ>> አልኳት በልምምጥ።

<<ምን አገባኝ! አሁን ከድር መምጫው ደርሷል!!>> ብላኝ ሄደች።

ቴዲ ያቀነቅናል እኔም አብሬው…

ይሄም በጥላቻ ይሄንን ሲወቅሰው
መለየት አቃተን የሚበጀንን ሰው።

ቴዲ አሁን በማ ሞት የሚመርጠውን መለየት አቅቶት ነው? ማንን ለመሸወድ ነው? የአልበሙን ፖስቸር ላይ የተነሳው ፎቶ አቋቋሙ (ሁለት እጆቹን ቀበቶ ማሰሪያው ላይ አሳርፎ ጭንቅላቱን ወደ ቀኝ ዘመም አድርጎ)  "ቅ" ፊደል  ሲሰራ ቅንጅትን የሚመርጥ መስሎኝ ነበር? ለካ ማንን እንደሚመርጥ ተወዛግቧል? እኔ ግን መለየት አላቃተኝም…ምመርጠውን  ለይቻለው…የምርጫ ካርድ ልወስድ ቀበሌ ስሄድ 18 አመት አይሞላህም አለኝ የመዝገብ ሹሙ…

<<የቁመቴ ማጠር አይተህ ነው? ቁመቴ የእርግማን ብዛት እንጂ የእድሜ አለመድረስ አይደለም>> ብዬ…አሳስቄ በስንት መከራ ነው ካርድ ያወጣሁት… መቼም ለካርዱ ይሄ ሁሉ ግብ ግብ የፈጠርኩት ያለውን አገዛዝ ለመምረጥ እንደሆነ ለናንተ መንገር አያሻኝም! ህእ!።

አቤት ስቃይ አቤት ጠኔ!
ሰማይ ጨክኖ በወገኔ።
ስንት አሳለፈንን…

ቴዲ ጠኔ ሲል በዛው ሰሞን ከጎረቤት ልጆች ጋር በአበላል አንተ ትበልጥ አንተ ትበልጥ እያልን የተከራከርነው ታወሰኝ።እኛ ቤት ቁጭ ብለን ስንከራከር ወንድሜ ከድር መደብ ላይ ቁጭ ብሎ እየቃመ ነፃት ጋዜጣን ያነባል።

<<አንተ ደረቅ በአበላል ከናንተ አልለይም ትላለህ? እንደውም አንድ ምክር ልስጥህ ሆድህ ውስጥ ፌስታል ይዞ የቆመ ደረሳ ሳይኖር አይቀርም  ሄደህ ሆድህን ተመርመር>> አለ አዚዝ ከደማቅ ሳቁ ጋር

<<ልክ ነው ተመርመር መቼ ለት ጉዱን ለማየት ሶስት ክትፎ ሰባህ ቤት አዝዤ አውድሞታል እኮ!!>>

<<የሰባህ ቤት ክትፎ ብዙ ኘሆኑ ነው?ቆርኪ በሚያክል ጣባ የሚያቀረቡትን ክትፎ ብዙ ነው ትላለህ? ብየ የመልስ ምቴን ቀጠልኩ… ስማ አንዋር !አዚዝ ከናንተ ጋር መከራከር የደንቆሮ ለቅሶ ነው ካላመናቹ ይኸው ከድርን ጠይቁት! ከናንተ የተለየ አበላል እንደሌለኝ ይንገራችሁ >>አልኳቸው።

<ህእ! ደረቅ በሚል ገፅታ አየኝ>> ወንድሜ ከድር።

<<አረ ከድር ስማው! አፒታይቴ ዝግ ነው ቆለፈኝ ይላል ወንድምህ!ባለፈው >> አለ አንዋር።

<<አረ በአላህ ከድር! ሀቁን አንተ አሳምንልኝ። ለሀቅ እኔ እበላለው? >> ስለው።በብርሃን ፍጥነት ከመደብ ላይ ዘሎ አጠገቤ ደረሰና። ሁለት እጆቹን እንደ ጉርሻ ወደ አፌ አስጠግቶ።

<<ከዚህ በላይ እኔን ልትላኝ ነው?  ና! ብላኛ ና!>>ሲለኝ።የተሳቀው ሳቅ መቼም አይጠፋኝም።

ከቴዲ ጋር አብሬ ማዜሜ ቀጥሏል።  (ይህቺ ፓርት ስሜቴን ስለምትኮረኩረው ድምፄን ጨምሬ በጩኸት አዜምኩ)

አልቅሰን ሳናባራ ብለይን ወይኔ!!
እዚህ ጋር ደግሞ ሌላ ትኩሳት…

ብዬ ሶፋው ላይ እየተንከባለልኩ በስሜት ባለኝ ድምፅ ሁሉ… ስቃጠል ወንድሜ … ገና ግቢ ሲገባ በስፒከሩ ድምፅ ተናዶ እሳት ለብሶ እሳት ጎርሶ ከች።

…ወገኔ አለቀ በወሲብ እሳት…
እሳት… እሳት…

በሩ በወንድሜ ተበረገደ…

<<አረ ባክህ አላህ እሳት ይልቀቅብህ አንተ ሰውዬ እሳት አትሁንብኝ!!>> ብሎ በምሬት ጮኸብ። ንዴቱ መልሱ በጣም አስቆኝ እየተንደፋደፍኩ ተነስቼ ሲዲውን እንዴት እንዳጠፋሁት አላውቅም። ፀጥ… ረጭ…!!

Monday, April 25, 2016

<<ጉዳዩ>>

ማሳሰቢያ:– 35% ግነትና ቅጥፈት።

  • ለመንደራችን ሁለተኛ ለመኖሪያ ቤታችን አንደኛ የሆነው ዘመናዊ "ጉዳይ" ዛሬ  በወንድሞቼ ታጅቦ ከቤታችን ይደርሳል። ጉዳዩ ቤታችን እስኪደርስ ከጊቢያችን በር ላይ ከአቻ ጓደኞቼ ጋር ተሰብስበን በናፍቆትና በጭንቀት በመጠባበቅ ላይ ሳለን…

"አኩም አልጄጆን?(አሁንም አልደረሱም)?" የሚለው የሴት አያቴ ድምፅ ከግቢው ውስጥ ተሰማኝ። ይሄን ጥያቄ ለሰላሳ ምናምነኛ ጊዜ ስትጠይቀኝ ነው!!

ለአፍታ ዞሬ በተሰላቸ ድምፅ

"አልደረሱም!" አልኳትና አይኔን ወደ ወንድሞቼና "ጉዳዩ" መምጫ  ጎዳና መለስኩ። መዘግየታቸው ህሊናዬን በሊሆን ይችላል ስጋት አጨናንቆታል… ወረሱት ይሆን እንዴ? ወይስ መንገድ ላይ የሚመጡበት መኪና ጎማ ፈንድቶ ይሆን? እያልኩ በጣም ተወዛግቤያለው። የአያቴና የጓደኞቼ አሰልቺና ተደጋጋሚ ጥያቄ ደግሞ ከመጠበቁ በላይ አዛ ያደረገኝ ጉዳይ ነው። መጠባበቅ ቋቅ እስኪለኝ ያሰለቸኝ አንሶ! ይነዘንዙኛል… ኡፋህ…

• ዛሬ ከቤታችን ይደርሳል የተባለው ጉዳይ ከሁለት ወር በፊት ነበር… ጅዳ  የምትኖረው አክስታችን ደውላ…"ጉዳዩን ልኬላቹሃለው ከጉምሩክ ሲደውሉላችሁ ሄዳችሁ ተረከቡ" ብላ ለትልቁ ወንድሜ በጎረቤት ስልክ የነገረችው።  ይህን ዜና መጥቶ ሲነግረን በአያቴ እልልታ በእህቴ ጩኸት በእኔ ፉጨት ቤታችን የኢያሪኮን ከተማ መሰለች። ቤተሰቡ ይህን ዜና ከሰማ ቅፅበት ጀምሮ  ወሬው  ስለ ጉዳዩ… ጉዳዩ… ጉዳዩ ሆነ። (በተለይ!! የእኔና የአያቴ  ወሬ…)

አያቴ በቡና ሰአት ለተሰበሰቡ ጎረቤቶች ከቡናው ጀባታ ቀጥሎ  ወሬዋ ሁሉ ስለ ጉዳዩ ጉምሩክ መድረስና በቅርቡ ቤታችን እንደሚደርስ… ማብራራት ነበር

"ለእኔ ለእናቷ ደስታ ብላ! ላቧን አንጠፍጥፋ እቁብ ገብታ ባጠራቀመችው ብር …  ከፋብሪካው ልክ እደተመረተ በትኩስነቱ… በውድ ገዝታ… በቶሎ ይድረስላት ብላ በአየር እጥፍ ከፍላ ነው የላከችልኝ…ጉዳዩ ብርቅ የሆነበት ጎረቤትም ጭንቅላቱን በአግራሞት እየነቀነቀ ያዳምጣታል።

አያቴ ቡና እንድትደግምላት ለእህቴ ሲኒውን እያቀበለች ማብራሪያዋን ቀጠለች …" ሴት ልጅ ናት መልበስ ማጌጥ ያምራታል፣ ፍላጎቷን ትታ እኔ እናቷ ደስ እንዲለኝ ብላ …  የለቅሶ ሳግ ማብራሪያዋን አደናቀፋት …

"ይተዉ እንጂ እማማ ይተዉ! እሷስ ያለ እርሶ ማን አላት! ለርሶ ደስታ ምንስ ብታደርግ ይበዛብዎታል እንዴ ? እንደውም ሲያንስዎ…ነው! የተመረቀች ክፉ አይንካት! እንዳስደሰተችዎ አላህ በባል በልጅ ያስደስታት! እርስዎ ብቻ ዱዓ ያድርጉላት!! እንጂ ውለታዋ ሲያንስዎ" አሉ እትዬ ዙበይዳ አያቴን ለማረጋጋት።
"እሱስ ልክ ነው…በዱዓውማ መች አሰቀርቼባት አውቃለው! … አለች! አያቴ ውለታው እንደማይበዛባት እየተስማማችና አይኖቿ ላይ የተጋገረውን እንባዋን በመቅረቢያዋ እየጠረገች። ቀጠሉ ጋሽ ጀማል…

"አይ ወርቅ! እንደሷ አይነት አስር ቢወለድ አይቆጭም! የተመረቀች! አላህ የመረቃት! አለች እንጂ የኔ እንከፍ… " አሉ ያጋመሱትን ቡና ፉት እያሉለት።

"አለች…እንጂ የኔ እንከፍ! ለስሙ ከአገር የወጣችው ከሰው ሁሉ በፊት ነው። አንድ ቀን እንደ ሰው አንድቀን!… ወላ ለኔ ሆነ ወላ ለእናቷ አንድ ጠቃሚ ነገር ልካም አታውቅ!! እርግጥ ነው አልክድም ሳታቋርጥ አንድ የምትልክልን ነገር አለ ለኔም ሆነ ለናቷ…  ።"አሉና  የስኒ ቡናቸውን አንስተው አገገባደዱ።

"ገንዘብ ነው ሳታቋርጥ ምትልክልዎ ጋሽ ጀማል?" ጠየቁ እትዬ ዙቤይዳ።

"ትቀልጃለሽ ልበል ዙበይዳ?"

"ታዲያ ምንድነው?"

"ነጋ ጠባ የምትልክልኝ?"

"እህ… !" አሉ በህብረት ። የሰዉ ጆሮ ሁሉ ወደ መልሳቸው ተቀሰረ።

"ህእ …አሉ ጋሽ ጀማል…በሹፈት…

ህእ…  ነጋ ጠባ ከሷ የሚደርሰኝማ  ደብዳቤ ነው።  ዛሬም ደብዳቤ… ነገም ደብዳቤ… ደብዳቤ በልተን የምናድር ይመስል። አንዳንዴማ በቃ ስራዋ ሁሉ ደብዳቤ መፃፍ ብቻ ይመስለኛል! እኔም ሆንኩ እናቷ በዚህ እድሜያችን የሚያስፈልገን ጧሪ ቀባሪ እንጂ! የብዕር ጓደኛ ነው እንዴ?…ነው ወይ? ብለው ጋሽ ጀማል ታዳሚው ላይ በልጃቸው ንዴት አፈጠጡ…

" ጉድ እኮ ነው! ልጄ ባይልላት እንጂ! በኛስ አትጨክንም! እርሶ ደግሞ" አሉ ባለቤታቸው እትዬ አለማሽ።

"አረ! ባይልላት…ነው?ተይ እንጂ?  ወገኛ!! ሌላው ይቅር የምትፅፍበት የወረቀትና የእስክሪቢቶውን እንኳ ብትልክልን ምናለበት? ለስሙ ልጅ ውጪ አለቻቸው መባሉ አልቀረ!!  ይኸውላችሁ አሁንማ የምትልከው ደብዳቤ ብዛቱ… ቤቴን ከመኖሪያነት ወደ መዝገብ ቤትነት ቀይሮታል!" ቤታችን ሳቅ ሞላው።

•  የድምፁ ጩኸት ለመላ ጎረቤት የሚሰማው የጎረቤታችን ስልክ ቂርርርርር አያለ  በተንጫረረ ቁጥር ቤተሰቡ መለ አካሉ ጆሮ ይሆናል። ከጉምሩክ የተደወለ እየመሰለን ጆሮአችን እንደ ባለጌ ጣት ይቀሰራል!!
አንድ ቀን ሁላችንም በተሰበሰብንበት ይሄ መከረኛ ስልክ ጮኸ…
ካሁን አሁን… ሊጠሩን ነው … ከጉምሩክ ነው … በሚል ጉጉት ሁላችንም መርፌ ቢወድቅ በሚሰማ መልኩ ባለንበት ቀጥ ፀጥ ብለን… ስንጠብቅ። የጎረቤታችን በር ተከፈትና በስልክ የተፈለገው ሌላ ሰው ስም ተጠራ።

"ኤጭ! ይሄ ደግሞ ከመደዋወል ሌላ ስራ የለውም እንዴ!?" ብዬ የተደወለለትን ሰው በሆዴ ቦጨኩት። በቤተሰቡ ሰፍኖ የቆየው ፀጥታ አበቃና … ወሬው ጀመረ… ስለሚመጣው ጉዳይ…

"ቆይ መቼ ነው የሚደውሉት?" ብላ ትጠይቃለች ታላቄ።

"ያው እስኪደውሉ መጠበቅ ነው!" ይላል መካከለኛው ወንድሜ አሊ።

አያቴ በስጋት "ጉርሙኮች ንብረት ይወርሳሉ! የሚሉትስ?"  ወይኔ ልጄ ሁሉ ይቅርብኝ ብላ የላከቸውን ብቻ… ስጋቷን… ሳትጨርሰው… ወንድሜ ጣልቃ ገባና…

"የሚወርሱት "ጉዳዩን" ሳይሆን ቀረጥ ሳይከፈልባቸው የተወዘፉ እቃዎችንና እቃና የሺሻ እቃ ነው"።

"የምንሻሽ እቃ??" አለች አያቴ።

"የሺሻ እቃ!"

"ምን አፈርን ኡሃንጋ? (ምንድነው እሱ ደግሞ? "

  ወንድሜ የሺሻ እቃን ለአያቴ የሚያስረዳበት ቋንቋ አምጦ አምጦ! በመጨረሻም… "ገመድ በመሰለ ትቦ የሚጨስ ሲጃራ ነው…!"
አለ።

"ይሄ እነ ሩቂያ አረቧ አንዳንዴ የሚያጨሱበት ነገር ነው?" አልኩት።

አንተ ነገረ ፈጅ! በሚል ግልምጫ አየኝና "አዎ" አለ በተገላገልኩ ስሜት።

• በእንደዚህ አይነት ካሁን ካሁን ደወሉልን ጉጉት ሁለት ወር ካለፈ ቡሃላ … ትላንት ከጉምሩክ ተደወለና ወንድሜ መጥተህ ውሰድ ተባለ። ጉዳዩን ለማምጣት በሌሊት ጉምሩክ ሄደዋል ሁለት ታላላቅ ወንድሞቼ

"ምንድነው አይደርሱም እንዴ?" አለኝ አቻ ጓደኛዬ አብዱ።

"ካንተ ጋር አይደለው እንዴ ያለሁት ምን እኔን ትጠይቀኛለህ?" እየተነጫነጭኩ መለስኩለት።

"እነ ከድር ከሄዱ ቆዩ ግን?" ሌላው ጓዴ ጀማል። እኚህ ሰዎች! አብደው ሊያሳብዱኝ ነው እንዴ?

"ሌሊት ቆማጣ ሳያራ ነው የሄዱት አላልኩህም!እናትንና! ካሁን ቡሃላ ብዬ ደግመህ ብጠይቀኝ አይንህን ነው በኩርኩም ምልህ ጅል!።" ብዬ ከዛቻ ጋር መለስኩለት።

"እንዴ የጠየኩህ አልመሰለኝማ!?" እያለ አጉረመረመ።

"በቃ ዝም በል! ጅብ አንጎል!።

ጀማል የሚመጣውን ጉዳይ በቤታቸው እንዳላይ ማዕቀብ ይጥልብኛል ብሎ ሰጋ መሰለኝ መልስ ሳይጨምር ዝም አለ።

   • ጥበቃው አታክቶኝ ወደ ግቢ ገባው። ግቢ በገባው ከአፍታ ቆይታ ቡሃላ… ጓደኞቼ በጅምላ  ሰላም… ሰላም… እያሉ ጠሩኝ ። ጉ ዳዩ መድረሱን አወኩ። ተርርር ብዬ ወደ ውጪ ወጣው። ቮልክስዋገን ፒካኘ መኪና ወደ ሰፈሬ … ጠ… ጠ… ጠ… ጠ… አያለች… መጥታ ግቢ በራችን ላይ ቆመች። የሰፈሬ ጎረምሶች መኪናዋን በመክበብ የ"ጉዳዩን" ደህንነት ወደላይ ወደታች እየተገለማመጡ ይቆጣጠራሉ። በኛ ጫጫታ ጎረቤት ሁሉ ለ"ጉዳዩ" አቀባበል ለማድረግ ግልብጥ ብሎ ወጣ። በደህንነት ጠባቂ ጎረምሶች ምንም አስጊ ሁኔታ አለመኖሩን የተረጋገጠላቸው ሁለቱም ወንድሞቼ ከመኪናዋ ዱብ ዱብ እያሉ ወረዱ። እልልልል… የወይዛዝርት እልልታ መንደሬን ቀወጣት። አያቴ ልጇን እንደምትድር እናት ወገቧን አስራ ጉድ ጉድ ትላለች፣ እህቴ ለጉዳዩ ቤት ውስጥ ቦታ ታስተካክላች። አኔ ከጓደኞቼ ጋር የአቀባበል ስነ ስርዓቱ ላይ በደስታ እንጫጫለን። "ጉዳዩን" ከመኪናው አውርዶ የወንድሞቼ መኝታ ክፍል ተሸክሞ ለማድረስ በፍትሃዊ ምርጫ … በድምፅ ብልጫ ከጎረምሶች ደንዳናው ተመረጠ። "ጉዳዩ" በተመራጭ ጎረምሳ መሀል አናት ተቀምጦ ጉዞ ጀመረ …  እኔና ጓደኞቼ ከጉዳዩ ከፊት ከፊት እየሄድን… "ዞር በሉ…መንገድ ልቀቁ!… መንገዱን ክፍት እናስደርጋለን።ከጉዳዩ ኋላ ተገልብጦ የወጣው ጎረቤት በደመቀ ሁኔታ አጅቦ ይከተላል።(የሁኔታው ድምቀት ታቦት ወደ ማደሪያው የሚሄድ እንጂ ጉዳዩ ወደቤታችን የሚገባ አይመስልም ነበር)። የሆነው ሆኖ ከአክስታችን የተላከው "ጉዳይ" ከሁለት ወር ጥበቃ ቡሃላ ቤታች ለመድረስ በቃ።

  • ከደማቁ የአቀባበል ስነስርአት ቡኃላ ጎረቤት ዘመድ አዝማድ ተበተነ። ጉዳዩም ከወንድሞቼ መኝታ ክፍል ተቀምጦ ተቆለፈበት። በትልቁ ቤት መላ ቤተሰቡ ተሰብስቦ በታላቅ ወንድሜ አፈ ጉባኤነት ስለ "ጉዳዩ" የአጠቃቀም በሁለቱም ወንድሞቼ የረቀቀው ህግና ደንብ ተነበበ። በወንድሞቼ ክፍል እንደሚያድር የተወሰነውን ጉዳይ ለማየት እኔና እህቴ በወንድሞቼ አልጋ ላይ ለአራት ለማደር ተገደድን። እንደዚህ በጉጉት በደማቅ በሀገር መሪ አቀባበል የተደረገለት፣እና ለማየት ጓጉተን አንድ አልጋ ላይ ለአራት ያስተኛን "ጉዳይ" ዛሬ ጊዜ ጥሎት እንደ ጠረጴዛ የመፅሀፍ መደርደሪያ ሆኗል…ጉዳዩ TOSHIBA እንጨት ለበስ  21" ባለ ቀለም TELEVISION ነበር።

ቀዩዋ ፖፖ…

    የ3 አመቷ የጎረቤቴ ልጅ ለይላ (አበሩ) እጇን በእናቷ ተይዛ ከመዋዕለ ህፃናት ስትመለስ ሳያት…አየችንና ሮጣ መጣች… ጉንጯን ስሜያት የት እንደምትማር ጠየኳት። የምትማርበትን አፀደ ህፃናት ስትነግረኝ ፈገግ አልኩ። ምክኒያቱም ከ 24 ዓመት በፊት እኔም በዚሁ አፀደ ህፃናቱ  ተምሬበታለውና… ወደ ድሮው ትውስታ በሀሳብ ነጎድኩ … ከአፀደ ህፃናቱ መዋያ በፊት በአይነ ህሊናዬ የሚታዩኝ ትውስታዎች የሚከተሉት ነበሩ…

  መርካቶ በሚገኘው መኖሪያ ቤታችን ግቢ ውስጥ ቢጫ ቁምጣዬን ለብሼ ስሮጥ ፣ስዘል፣ ሰፈራችን ላይ በቆመ ከባድ መኪና መውጣት ተስኖኝ ጎማው ስር ስርመሰመስ … ከጓደኛዬ አብርሃም ሰርጉ ጋር… "ደርግ ያሳደገው ሌባ ፣ ኢህዴግ ይቀጣዋል" እያልን ስንዘምር፣ ደግሞ ስንሯሯጥ "ጩሎ ትትሰበራ!" የሚለው የአያቴ የማስጠንቀቂያ ድምፅ። ከ ጓደኛዬ አብርሃም ና ጀማል ጋር ከቀዩ አፈር ግድግዳ ላይ አፈር እያረጋገፍን ስንቅም ፣ከሌላ ጓደኛዬ ከሄኖክ ጋር ስንደባደብ ሲያሸንፈኝ መልሰን ስንሻረክ… ከቤት ስላክ "አልሄድም ሀምዱ ይመታኛል!" ስል (ሀምዱ እያነበብክ ነው?)  ደግሞ ያቺ ቀዩዋ ፖፖዬ ላይ በእግሬ እየተጫወትኩ ለእዳሪ ስቀመጥ…

ወይኔ! ቀዩዋ ፖፖዬ… (እሷን ያስጣለኝ… የጳውሎስ ኞኞ ትዕንግርት የሚለው መፅሄት ነበር…መፅሄቱ እንዴት እንዳስጣለኝ መጨረሻ ላይ እመለስበታለው።)

የመዋዕለ ህፃናቱ ትውስታዬ የሚጀምረው ከዚህ ነው…

   በአይን አባቴ ጋሽ ሼሂቾ ስፖንሰርነት ከትልቋ እህቴ (መይሙና) ጋር ሄጄ መዋዕለ ህፃናት ተመዘገብኩ። ትምህርት በተጀመረ ቀን እህቴ (መይሙና) አንድ እጄን ይዛኝ … በአንድ እጄ የምሳ እቃ አንጠልጥዬ ፣ በጀርባዬ ቦርሳ አንጠልጥዬ ፣ ደረቴ ላይ በመርፌ ቁልፍ የተያዘ መሀረብ አንጠልጥዬ፣ ከህፃናት መዋያው በር ደረስኩ። መግቢያ በሩ "እንቢ! አንገባም!"  በሚሉ ቁጫጭ ህፃናት ሁካታና ጫጫታ ተቀውጧል። (ነገርየው የግዞት እስር ቤት ነው እንዴ?) የህፃናት መዋያው ጥበቃ (ትዝ ይለኛል አውራጣቱ ቆራጣ ነበር!!) አንገባም ያሉ ቁጫጮችን እየዘገነ ወደ ቅጥር ግቢው ይወረውራቸዋል። ይህን ሳይ የመግባት ሞራሉን አጣውና ፈራው! አልገባም! ብዬ  ልቀውጠው አልኩና የሚገጥመኝን በቆራጣ እጅ የመወርወር ዕጣ ፈንታ አስታውሼ… በከፍተኛ ድብርት እንደ ኤሊ እየተንቀራፈፍኩ ወደ በሩ ተጠጋው በር ጋር ስደርስ። ከኋላዬ ራቅ ብላ የቆመችው እህቴ "ቡሃላ አስረስ መጥታ ትወስድሀለች እሺ!" አለችኝ። ምን አማራጭ አለኝ በሚል እይታ አይቻት ወደ ውስጥ ዘለኩ።

  … ግቢው በምድረ ዉሪ ተሞልቷል። ነባር ተማሪዎች አንድ አይነት የኑፎርም ለብሰዋል እንደኔ አዳዲስ ተማሪዎች ደግሞ የክት ልብሳቸውን ለብሰው በረድፍ ረድፍ ተሰልፈዋል። የምሰለፍበትን ረድፍ በአስተናባሪ መምህራን ተጠቁሜ ከአንዱ ሰልፍ ተቀላቀልኩ። ከሰልፋችን ፊት ለፊት ከፍ ባለ ቦታ ላይ (መድረክ መሆኑ ነው) ሙሉ ልብስ የለበሰ ሰው ንግግር አደረገ … ቀጥሎ አስቂኝ የአሻንጉሊት ትርዒት እንደሚቀርብ አስተዋውቆ ወረደ። አስቂኝ አሻንጉሊት የተባለው ነገር መድረኩ ላይ ወጣ። በህይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ ከፍርሃት ጋር የተዋወኩት በዚህች ቅፅበት ሆነ… ጠላታችሁ እንደዚህ ክው ይበል! እቤት ሳስቸግራቸው "ጭራቅ መጣልህ" እያሉ የሚያስቦኩኝን ጭራቅ ስጋ ለብሶ ከፊቴ ቆሞ በአይኔ በብረቱ ያየው መሰለኝ ፈራው።

  ወ ተተኘኘረዞቀ
@… ለአይኑ ብቻ ቀዳዳ ባለው ጥቁር ጨርቅ ከአናቱ ጀምሮ ቁመቱን እስካስረዘመበት እንጨት ድረስ የተከናነበ ሰው ነበር። ፈጣሪ ይይላቸውና! ይሄንን ነበር እንግዲ ለኛ ለደቂቅ ህፃናቱ አስቂኝ ነው ያሉን አሻንጉሊት።  አንደዛ ሆኖ ሲኮምክ ከማሳቅ ይልቅ እኔን ጨምሮ ብዙሃን ህፃናቱን በፍርሃት አሳቀቀን!። እኔማ ቢጨንቀኝ ቢጠበኝ ማሳቀቁን ጨርሶ እስኪወርድ አይኔን ከሱ ላይ አሸሸው። ጨርሶ ወረደ። ኡፍፍ ግልግል!!። እዚህ ያመጣችኝ እህቴን መውቀስ ቃጣኝ…  አሳቅቀው ከጨረሱን ቡሃላ ወደየ ክፍሎቻችን ገባን። ክፍሉ ውስጥ  እንደራሳችን ትንንሽ የሆኑ ወንበርና ጠረጴዛዎች ተቀበሉን። የክፍሉ ግድግዳ ዙሪያ በጣውላ በተሰራ መደርደሪያ ላይ አለፍ አለፍ ብሎ አሻንጉሊቶችና መጫወቻዎች ተደርድረዋል። መደርደሪያው እጅግ ከፍ ተደርጎ ስለተሰራ አሻንጉሊቶቹን ልናያቸው እንጂ ልንዳስሳቸው አንችልም ነበር። አንዱን ወንበር መርጬ ተቀመጥኩ… የተለያዩ መምህራን እየተፈራረቁ ራሳቸውን አስተዋወቁን…  በየአንዳንዳቸው… ሀሁሂሃ… 1234… ABCDE… በተራ ተራ ተማርን።

  እማማ ጅማቴ (የህፃናት መዋያው የፅዳት ሰራተኛ) እጃቸው ላይ… ኪሊሊሊሊሊ…  የምትል ቃጭል አንቃጭለው የእረፍት ሰአት መድረሱን አወጁልን። ከክፍል ወጣው… ከምንም አይነት ተማሪ ስላልተግባባው ለጊዜው ብቸኛ ሆንኩ። ደበረኝ! ምናልባት ከቤተሰብ ተለይቼ ስውል የመጀመሪያዬ ቀን ስለሆነ ይሆናል። ከግቢው አንድ ጥጌን ይዤ እንደ ሁሉም አዲስ ተማሪዎች በእንግዳነት ስሜት ሁኔታውን እታዘባለው። እንደልባቸው የሚሯሯጡት የሚጫወቱት የሚዘሉት ነባር ተማሪዎች ብቻ ናቸው። ከውሃ ቧንቧው አቅራቢያ የተወሰኑ ህፃናት በማይታየኝ ነገር ላይ እየተጠቋቆሙ ሲያሾፉና ሲስቁ አየው። ምን ይሆን ብየ ለማየት ሄድኩ…። ልብሳቸው ላይ እዳሪ ያመለጣቸው ቁጫጮች በእማማ ጅማቴ ቂጣቸውን እየታጠቡ ነበር። ልጆቹን እንደዛ ያሳቃቸው ቂጥ ማየታቸው መሆኑ ገረመኝ … (ያሳቃቸው እብደት ወይስ … ፍደት ?) ሳቅ ብዬ አይኔን ወደሌላ አቅጣጫ ወረወርኩ። በፍርግርግ ብረት በር የተቆለፈበት ህፃናት መዋያው ውስጥ ያለ ሌላ ግቢ ተመለከትኩ። በሩ አካባቢ አጮልቀው የሚያዩ ልጆች አሉ። ተጠግቼ ሳይ በሳር በአበባ አና በልጆች መጫወቻ የተሞላ መናፈሻ ነው…! ዥዋዥዌ ፣ሸርተቴ፣ መሸከርከሪያ ምናምን (የኛ ዘመን ኤድናሞል በሉት)። መዋያው ከገባው ለመጀመሪያ ጊዜ የተደሰትኩት በዚህች ቅፅበት ነበር። ደስታዬ ብዙም አልቆየም የመጫወቻ ግቢው የተቆለፈበትን ቁልፍ ሳይ ለመጫወት የነበረኝ ጉጉት በኖ ጠፋ…በመዋያው በቆየሁበት ሁለት አመታት ውስጥ መጫወቻዎችና አሻንጉሊቶች ከማየት ባለፈ በተግባር መጫወት አልቻልንም።  ለምን አንደሆነ ዛሬም ድረስ መልስ ያጣሁለት እንቆቅልሽ ነው።

ከዕረፍት መልስ ትንሽ ተምረን በእማማ ጅማቴ ቃጭል ብስራትነት ለምሳ ተለቀቅን። የምሳ ዕቃዎቻችንን ከሚቀመጡበት ስፍራ የራሴን እንስቼ  በግቢው ጥላማ ቦታዎች አንዱ ጋር ተቀምጬ ምሳዬን በላው። ከምሳ ቡሃላ ባለው ጊዜ መተኛት እንጂ መማር የለም። ጠዋት ደብተር አስደግፈን በተማርንበት ጠረጴዛ ላይ ከሰዓት ቡሃላ ከደረታችን በላይ ያለ አካላችንን አስደግፈን እንተኛበታለን። (የዛሬ ዘመኖቹ ፍራሽ አላቸው አሉ!)።ህፃናት  መዋያው መዋል በጀመርኩ የተወሰኑ ቀናቶች ውስጥ ትንሽ ትንሽ ተላመድኩ። ዛሬ ላይ ማላስታውሳቸው ጓደኞችንም ያዝኩ።

  አንድ ቀን በምሳ ሰዓት ላይ ችግር ገጠመኝ። ምሳዬን ለመብላት የምሳ እቃዬን አንስቼ ከለመድኳት ስፍራ ተቀምጬ። የምሳ አቃ ክዳኑን ለመክፈት አሽከረከርኩት ከወትሮው ጠበቅ አለብኝ። ሀይል ጨምሬ በትግል ከፈትኩት። ውስጡ ያለውን እንቁላል በዳቦ ሳይ ደነገጥኩ። ያስደነገጠኝ እንቁላል ተቋጥሮልኝ ስለማያውቅ አልነበረም። የዛን ዕለት ጠዋቱን ግን  እህቴ የቋጠረችልኝ እንቁላል እንዳልነበር ስላወኩ እንጂ። አይ በቃ እህቴ ደስ እንዲለኝ በመሃል መጥታ ምግቡን በእንቁላል ቀይራልኝ ይሆናል ብዬ። በእህቴ እንክብካቤ እየተደሰትኩ። ቡሃላ ሳገኛት እንዴት አቅፌ ጉንጯ ላይ  እንደምስማት እያሰላሰልኩ እንቁላሉን መከትከት ጀመርኩ። ጉድና ጅራት ከኋላ ነው እንዲሉ ከዚህ ቡሃላ ነበር ጉዱ የተከሰተው። እየበላው ሳለ … አንድ ተማሪ ከአንድ መምህር ጋር ወደኔ አቅጣጫ ሲመጡ አየው። ተማሪው የኔን አይነት የምሳ እቃ በእጁ አንጠልጥሏል። የዚህን ጊዜ ነበር አንድ ስህተት መፈጠሩን ደመነብሴ ሹክ ያለኝ። አጠገቤ ሲደርሱ ከአይኔ ብቻ ቀና ብዬ አየዋቸው።

ልጁ "ይሄ ነው የኔ ምሳ ዕቃ ብሎ" ወደ ምበላበት የምሳ እቃ ጣቱን ቀሰረ። (እናቱንና! ጣቱን ብነክሰው ደስ ባለኝ።)

"ለምን የሰው ምሳ እቃ አነሳህ?" አለችን መምህሯ። ድንብርብሬ ወጣ!

"የራሴ መስሎኝ ነው!" አልኩ አፌን ዳቦ በእንቁላል በሞላሁበት አንደበቴ እየተኮላተፍኩ።

  እርግጥ ነው የምሳ እቃዎቹ መመሳሰል እንደ አህያ ለመለየት የሚቸግር ነበር። ይህን የተረዳችው መምህሯም "ለሌላ ቀን ሁለታችሁም ስማችሁን ፃፉበት" ብላ። ያጋመስኩትን ምሳ እቃ አንስታ የኔን አስቀምጣ ሄደች። ምሳ ዕቃዬን ለመክፈት ወኔው ጠፋብኝ። እንቁላል እንዳልተቋጠረልኝ ባውቅም በሆነ ተዓምር እንቁላል እንዲሆንልኝ ተመኘው። ከአንቁላል ወደ እንጀራ በወጥ ወደ ኋላ መመለሱ እየሸከከኝ ክዳኑን ሳሽከረክረው ሳያታግለኝ ተከፈተ። አይ በቃ! እንጀራ ነው እንቁላል ቢሆን በደንብ አጥብቃ ትዘጋው ነበር…  የፈራሁት አልቀረም እንጀራ በወጥ… ሆኖ ተገኘ። ከባድ የአፒታይት መቆለፍ ተከሰተብኝ። አሳይቶ መንሳት ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ተረዳው።

☞ ቅድም እህቴን እንዴት ጉንጯን እንደምስማት ያቀድኩትን ዕቅድ!…  እንዴት አድርጌ ጉንጯን እንደምነክሳት በማቀድ … ቀየርኩት!! Kkkkk

   • ስለ ቀዩዋ ፖፖዬና በሷ መቀመጥን ስላስተወኝ የጳውሎስ ኞኞ ትዕንግርት መፅሄት ልንገራችሁና እትትዬን ልቋጭ።

   በልጅነቴ የግሌ ንብረት ከምላቸው ቁሶች ውስጥ አንዷ ቀዩዋ ፖፖዬ ነበረች። በዚህች ፖፖዬ ስቀመጥ ደስ ይለኛል። ነፃነት የተባለ ሁሉ በመዳፌ ያለ ያህል ይሰማኛል።በዙፋን ላይ የተሰየምኩም ጭምር…  ይሄ ስሜት ያለ ምክኒያት አልተከሰተም። በእሷ  ከተቀመጥኩ "ና ይሄን እቃ" ይዘህ "ና ሼኪ ሱቅ ሂድ" የለ መላላክ የለ። ለዚህም ነበር ቶሎ ልፋታት ያልቻልኩት። ይሄን ፖፖ የሙጥኝ ማለቴን የሚያውቀው ታላቅ ወንድሜ(ከድር) አንድ ቀን በዚህችው ዙፋኔ ላይ በተቀመጥኩበት በአይኑ ገርምሞኝ አልፎኝ ወደ ቤት ገባ። ሲመለስ እጁ ላይ ትዕንግርት የተሰኘውን የጳውሎስ ኞኞን መፅሄት ይዞ ነበር። (ይህ መፅሄት እስከ ቅርብ ጊዜ እጄ ላይ ነበር)። አጠገቤ ደርሶ ሊያሳኝ የፈለገውን ገፅ እየገላለጠ መፈለግ ጀመረ። የሚፈልገው ገፅ ሲደርስ…

መፅሄቱን እያቀበለኝ "ይህን ፎቶ ተመልከተው…! አለኝ።

  በተቀመጥኩበት ተቀብዬው ፎቶውን አየሁት። ፍቶው (አንድ ድመት በሽትቤት መቀመጫ ሴራሚክ  ላይ ተቀምጣ)ነበር። በአፍረት አንጋጥጬ በአፍረት አየሁት

"ድመት እንኳ ሽንትቤት በምትጠቀምበት ዘመን! አንተ ዘላለም አለምህን ፖፖ ላይ ትቀዝናለህ? ቀሽም!" ብሎኝ ብቻ ሄደ።

  በድመት መበለጤ ከነከነኝና ከዛን ቀን ቡሃላ  ከፖፖዬ ጋር ተለያየን። የታላቅ ወንድሜ ሳይኮሎጂ ሰራ። ፖፖዬ ስራ ፈታች። ጊቢ ውስጥ ተጥላ ተጉላላች… ይህን የተመለከተች መካከለኛዋ እህቴ (ሽትዬ ወድሻለው) አነሳቻትና አፈር ሞልታ አበባ ተከለችባት። አይ ልጅነት!!

Wednesday, April 20, 2016

"የመጨረሻው ሳምንት" እውነተኛ ታሪክ

     ጊዜው ከ12 አመት በፊት ነበር…በኮልፌ የእስላም መካነ መቃብር ለቀብር ዚያራ ሄድኩ። ጊቢው ውስጥ… ከቀኝና ከግራ የተዘረጋውን ደናማ መካነ መቃብር ከዋናው በር ጀምሮ እስከ መጨረሻው ሰንጥቆ የሚዘልቀውን አስፓልት መንገድ ይዤ ተጓዝኩ። ወደ 30 ሜትር ወደ ውስጥ እንደዘለቅኩ ዛሬ "ሳይሰገድብህ ስገድ" የሚል አስጠንቃቂ ማስታወቂያ ከተለጠፈበት እድሜ ጠገብ ዛፍ አካባቢ ስደርስ ወደ ቀኝ ታጠፌ ግንቡ ጫፍ ያለውን የአያቴ ቀብር ደረስኩ።

ሞት ለሰው ልጅ ጊዜውን ጠብቆ የሚገጥምና ፈፅሞ የማይቀር ፅዋ ነው። ለሞት እጁን ማይሰጥ ለሞት የማይንበረከክ ለሞት የማይበገር ህያው ፍጡር የለም። በዚህም መሰረት የአያቴ ጊዜዋ ደርሶ ከሙታን ማህበር ተቀላቅላለች። ከሳምንት በፊት አያቴን ስንቀብር  ከቀብሩ አለፍ ብሎ የነበረው ባዶ መሬት በአዳዲስ ቀብር መሙላቱ አስገረመኝ … ከምኔው ሞላ? …ጉድ!በሚል ተገርሜ… በልጅ ልሳኔ ለአያቴ ብሎም ለሁሉም ሟቾች ፀሎቴን ለራሴ ብቻ በሚሰማ ድምፅ አደረስኩ…

አያቴ ቀብር ዙሪያውን በአምስት የህፃናት ቀብር መከበቡን  የታዘብኩት በዚያች ቅፅበት ነበር። ይህን ስመለከት…በአያቴ ለቅሶ ላይ አንዲት ጎረቤታችን ለለቀስተኛው ሰው አያቴን በተመለከተ አየሁ ብላ የተናገረችው ህልም ፊቴ ላይ ድቅን አለብኝ። ህልሟና አያቴን የከበበው የህፃናት ቀብር እጅጉኑ ተመሳሰለብኝ አስገረመኝም አስደነቀኝም። …ጎረቤታችን አየሁት ያለችው ህልም በአጭሩ እንዲህ ነበር…"አያቴ በሚያለቅሱ ህፃናት ተከባ በተራ በተራ እያቀፈች ፣ስታባብላቸው ስታጫውታቸው… ዘወተር እሮብ እንደምታደርገው አተካኖ ስታበላቸው…"ነበር።

☞(አያቴ ዘወትር እሮብ ወይ ሀሙስ ነጭ ቶቧን ለብሳ፣ አተካኖ ወይም ቆጮና አይብ ሰርታ ፣ እንስራ በሚያክል በግድንግድ ጀበና ቡና በቅቤ አፍልታ ፣መላ ጎረቤት ተጠርቶ እየተበላ ቡና የሚጠጣበት… በቡናው ያልተገኘ ቋሚ ታዳሚ ሰው ድርሻው ሳይነካ የሚቀመጥለት… ሲመጣ ድርሻውን የምትሰጥበት የቡና ሴሬሞኒ ልምድ ነበራት)

በአምስት ህፃናት ተከባ የሚለው ህልም በአምስት የህፃናት ቀብር ቀብሯ መከበቡ የሚያመሳስለው ነገር እንዳለው መቼም ግልፅ ነው… ሚስጥሩ ግልፅ ባይሆንልኝም ይህ ነበር ያስገረመኝ። እዛው ቀብር ቆሜ… የህልሙ ግርምት ወዳለፈው የአያቴ የመጨረሻ ሳምንት በትዝታ ወሰደኝ…

የሳምንቱ እረፍት በሆነ እሁድ ቀን እንደ እናት ካሳደገችኝ አያቴ ጋር አስኮ ከምትኖረው ታላቅ እህቴ ቤት ውለን ወደ መርካቶ ስንመለስ። ከወትሮው በተለየ እርጋታ እንደ ትልቅ ሰው ያየችውን ህልሟንና ተከትሎ የመጣውን ሀሳቧን ታማክረኝ ገባች። በጊዜዉ እኔ እድሜዬ የአስራዎቹ አጋማሽ ስለነበርና ልጅነት ስለነበረብኝ እና ያን ያህል ለቁምነገር ብቁ ስላልነበርኩ ከዚህ ቀደም እንደ አዋቂ አወያይታኝ አታውቅም ነበር… የዛን እለት ግን። እኔን ለቁም ነገር አጭታ ማወያየቷ ገርሞኛል። በውስጤ አዋቂ ሆንኩ ማለት ነው ብዬ የአዋቂነት ስሜት ከደስታ ጋር ተሰምቶኝ የምትለውን በፅሞና አዳምጣት ጀመር…

"ሰሞኑን ህልም አይቻለው…"ካቻምና የሞተው ልጄ በመኪናው አንድ ስፍራ ድረስ ወስዶኝ መኪናውን አቆመና <<ያንቺ ቦታ እዚህ ነው ውረጂ>> ብሎ ከመኪናው አውርዶኝ ሲሄድ አየሁ አለችኝ።
ህልሙ በሚስጥር አንዳች መልዕክት ያስተላለፈላት ይመስል… በዚህ ሁለት ቀን ገጠር ልጄ ጋር(እናቴን ማለቷ ነው) ደርሼ እመጣለው ማስተካክልላት ነገሮች አሉ ስለዚህ የቤቱን አደራ!" አሁን ልጅነት የለም…ትልቅ ሁነካል ብላ ከዚህ ቀደም ብላኝና  አድርጋ የማታውቀውን አደራ ጣለችብኝ። ለነገሩ በቤቱ እኔና አያቴ ብሎም የምግቤቱ ሰራተኞች ብቻ ነበር የምንኖረው። ቢሆንም ከዚህ ቀደም ገጠር ለመሄድ ስትነሳ ከሰራተኞቹ ዋናዋን ነበር አደራ ብላ የምትሄደው።

  በሁለተኛው ቀን ማክሰኞ እንዳለችውም ወደ ገጠር ሄደች። በአያቴ አደራ መሰረት የዛን ሰሞን የቤቱ ጥበቃ በእጄ ላይ ወደቀ። በዚህ አጋጣሚ አያቴ ስትመጣ ሰርኘራይዝ ላድርጋት በሚል ቤቱን አፀዳዳው። ልብሶችን በሙሉ አሳጠብኩ። አንዳንድ ቁሶችን ቦታ በመለዋወጥ የቤቱን ይዘት አሰፋሁት አሳመርኩት። ቤቱ የተለየ ድምቀት ተጎናፀፈ። ብርሃነን በብርሃን ሆነ።  የአያቴን አልጋ ዙሪያውን በትልቅ መጋረጃ ጋረድኩት። ለምን እንደዛ እንዳደረኩ አላውቅም። ይህን ሳደርግ… እህቴና የወንድሜ ሚስት ተያይዘው ወደ ቤትገቡ። ከሰላምታ ልውውጥ ቡኋላ…

"እንዴ ቤቱ እንዴት ሰፋ አማረ? ደግሞ መጋረጃው ምንድነው? "ሲሉ አደናቆትና ጥያቄ አከታተሉብኝ።

"እማዬ ሰሞኑን ሙሽራ ነች!"ለዛ ነው የጋረድኩት ብዬ በመቀለድ ያላሰብኩትን መልስ ሰጠዋቸው።

"አረ ይደብራል አንሳው"!አሉኝ። እሺ አልኩ ነገር ግን አላነሳሁትም።

መጋረጃውን በተመለከተ በርካታ ሰዎች ቢጠይቁኝም። መልሴ "እማዬ ሰሞኑን ሙሽራ ነች!" የሚለው ብቻ ሆነ። ዛሬ ላይ ሆኜ ሳስበው እንደዛ መልስ እመልስ የነበረው እኔ ሳልሆን… የአያቴን የዛን ሳምንት ዕጣ ፈንታ ያወቀ አንዳች ነገር በኔ ምላስ የመለሰው መልስ ይመስለኛል። የመልሴ ሚስጥር ግልፅ የሆነልኝ ከሳምንት ቡሃላ ነበር። በዛን ሰሞን የአያቴ አደራ ለመጠበቅ የምግቤቱን ሂደትና ሂሳብ በቅርበት ለመከታተል አብዛኛውን ሰአት ቤት ውስጥ አሳልፍ ነበር። ከአንድም ሁለት ሶስት ሰው አያቴን ፈልጎ ቤት ድረስ መጣ። እንዴ ሰው ምን ሆኖ ነው ሰሞኑ አያቴን አጥብቆ የፈለገው?  ወይስ እኔ ሳላውቅ አያቴ ህጋዊ ጠበቃ ወይም የምክር አገልግሎት መስጠት ጀምራለች? ብዬ ለራሴ በጥያቄ መልክ …ቀለድኩ።

(ከጊዜ ቡሃላ ነበር ሰዎች አያቴን ፈልገው መጥተው የነበረው … ሁሉም ስለ አያቴ አስጊ ህልም አይተው ሊነግሯትና ዱዓ አድርጉ ሊሏት መሆኑን ያወኩት)

  አያቴ አርብ ከቀትር ቡሃላ ከገጠር ጓዝ ሳታበዛ ቀለል ባለ ሁኔታ መጣች። የተለየ እርጋታዊ ሞገስ ይታይባታል። ጎረቤት በመላ እየዞረች ሰላም አለች።(ከዚህ ቀደም ከገጠር ስትመጣ ይህ በገጠመኝ እንጂ ሆን ብላ በየቤቱ ዞራ ሰላም አትልም ነበር) ስትመጣ ለብሳው የነበረውን ልብስ አውልቃ አሁኑኑ ይታጠብ አለች። ቡና ተፈልቶ ቤቱ ደመቅመቅ አለ። ስለ መጋረጃው  ጠየቀችኝ። እንደተለመደው። "ሰሞኑን ሙሽራ ነሽ" እኮ ስላት ፈገግ አለችና… እራት ቀረበና ተበልቶ መጨዋወት ጀመርን … ገጠር ስላሳለፈችው ሁኔታ ያሰበችው እንዳሳካች እንዳስተካከለች … እናቴ አንድ ቀን እደሪ ብላ ብትለምናትም አይሆንም ብላ መምጣቷን…ሌላም ሌላም ነገር ተጨዋወተን ለመኝታ መዘገጃጀት ጀመርን። አያቴም በመጋረጃ ከጋረድኩላት አልጋዋ ተኛች። ሁላችንም በየመኝታችን ደቀስን። ከመጋረጃው ውስጥ የአያቴ ድምፅ ተሰማኝ"የበላችው እራት እንዳልተስማማት ተናገረች" ምን እንደሆነ ያልተረዳሁት ፍርሃት ፍርሃት አለኝ።

የሌሊቱ ፅልመት መጥራት በሚጀምርበት ማለዳ…ላይ አያቴ ትን እንደማለት ሲላት ሴቶቹን ቀስቅሳ የሚጠጣ ውሃ ስጡኝ ብላ ከአልጋዋ ወርዳ  ምንጣፍ ላይ ተቀመጠች። ሴቶቹ በፍጥነት ሁሃ አምጥተው አቀበሏት… የጠጣችው ውሃ አልወርድ አላት… ልጄን ጥሩት ልጄን ጥሩት ብላ ወደተኛሁበት አመለከተች… የሴቶቹ የህበረት ጥሪ ከእንቅልፌ አባነነኝ…ቀና ብዬ ስመለከት አያቴ በተጨነቀ ገፅታ … በእጇ ና ና…ቶሎ በል… በማለት ጠራችኝ። እየሮጥኩ ሄጄ ደግፌያት በድንጋጤ"እ… እማ ምን? ምንሆንሽ? " ስላት… ልትነግረኝ የፈለገችውን ለመናገር አንደበቷ ከዳት… መናገር አለመቻሏን ከፊቷ ገፅታ ተረዳው… የእስትንፋሷ ማመላለሻ ትቦ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መዘጋቱን የመጨረሻው  ክርርር የሚለው የትንፋሿ  ድምፅ አረዳን…ያለምንም ህመምና ጣር በሚስጥራዊ ህልም ጋጋታ ብቻ የተጠናቀቀው የአያቴ የምድር ቆይታ የመጨረሻ ሳምንት  ትውስታው ይሄን ይመስላል።

አላህ ጀነተል ፊርደውስ ይወፍቃት!