Monday, September 26, 2016

"ል ጅ አ ል ባ ው አ ባ ት"


   … የዛሬ ልጆች የሚሸኑበት ዳይፐር በየቀኑ ሲገዛላቸው፣ እኛ የምንሸናበት ድርብና ሶስት መዓዘን የነጠላ ጨርቅ በየቀኑ ይታጠብል ነበር።የዛሬዎቹ ፊደል የሚቆጥሩት ደብተር በሚያክል ተች አስክሪን ስማርት ፎን ሲሆን፣እኛ የፊደል ገበታ የቆጠርነው ደብተር በሚያክል ካርቶን ላይ በተለጠፈች የፊደል መማሪያ ነበር። የዛሬ ልጆች የሚዝናኑት ኤድናሞል፣ እነ ቦራ በሚባሉ ዘመን አፈራሽ አስደሳች መጫወቻዎች ባሉባቸው ስፍራዎች ሲሆን፣ እኛ አንበሳ ግቢ፣ በፍርግርግ ብረት የተከረቸመባቸው አስፈሪ  አንበሶች ሲያዛጉና፣ ሲያገሱ በማየት ነበር። ያም ሆኖ ልጅነቴን ናፍቃለው። ከዘመኑ ልጆች ጋር ልዩነታችን ወሰኑ የሚለያይ ቢሆንም ቅሉ፣ በመጠኑም ቢሆን እነሱን መመልከት ወደ ልጅነቴ የትዝታ ባህር ይሸኘኛል…
•••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••

  ርዕስና መግቢያውን አንብበህ፣ ልጁ ምን ነካው ? ወፈፍ አደረገው እንዴ? ምን ይዘላብዳል ብለህ ይሆናል?። ግድ የለም አትጨነቅ! እኔ ምንም ወፈፍ አላደረገኝም፣ ወይም በደብተራ መተት ህሊናዬም አልሳትኩም። ግን እመነኝ ልጅ አልባ አባት ሆኛለው። እንዴት ሳትወልድ አባት ሆንክ? ካልከኝ። መልሴ ላልወለድኩት ልጅ የአባትን ፍቅር በሚያስንቅ መልኩ ፍቅር በመስጠቴ ሰበብ፣ የሚለው ይሆናል። ቆይ ግን ሰው ሳይወልድ እንዴት ከወላጁ በላይ ለልጅ ነጋጠባ አንጀቱ ሊንሰፈሰፍ ይችላል? አይገርምህም?  በህይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ የገጠመኝ ትዕንግርት ቢኖር ይኸው ነው።

ሚሩ የሚባል የስድስት አመት ልጅ የህይወት አጋጣሚ አገናኘችን። በቃ ካወኩት ጀምሮ ለሚሩ ከአባት እናቱ በበለጠ መልኩ፣ ስለ ደህንነቱ ማሰብ፣ ስለ ጤንነቱ መጨነቅ፣ ስለ ሳቁ መመኘት፣ ስለ ሀዘኑ መንሰፍሰፍ፣ ጀመርኩ። ይገርምሃል ሚሩ ድንገት ራበኝ ካለኝ ያሳዝነኛል። እይኔ ላይ እንባ ግግር ይሞጀራል፣አንጀቴ ይላወስለታል። ምግብ አስልኬ እስኪመጣለትና እስኪበላ፣ ውስጤ ይንቆራጠጣል። ሳይበላ ቀርቶ አይደለም ከናቱ ጋር ጥብስቅ አድርጎ ቢበላም፣ ልጅ ነውና ሲሮጥ፣ ሲዘል ሲጫወት የበላው ወዲያው ብን ይልበታል። ይህ ሁኔታዬን ተረድቶ ባይርበውም ፍላጎቱን ለማሳካት ራበኝ ይለኛል፣ እንደዋሸ ብነቃበትም እውነት ለማስመሰል የሚያደርገው ጥረት ደግሞ ይበልጥ ያዝናናኛል። ወደ ልጅነቴ ትውስታ ያነጉደኛል። በዚህም የመጣ፣  ልጅ የሌለው አባት ሆኜልሃለው። ገና ሳልወልድ የአባትነት ፍቅርን ማየት ችያለው።

በአንድ እለት አዛው ስራ ቦታ በአንድ ሰው ምሳ ተጋበዝኩ፣ ሚሩን አስከትዬ መሄድ የተጋባዥነት ሞራሌ ይሉኝታ በሚሉት ገመዱ ተብትቦ አሰረኝና ሚሩን ትቼ ለመሄድ ተገደድኩ። ከጋባዤ ጋር ተያይዘን ከሚሩ ራቅን፣ ውስ ጤ ጥዬው ልበላ በመሄዴ፣ የወቀሳአይነት ይደረድርባኛል። ሆዴን ባርባር እያለው ሄድኩ፣ ሚሩ ከአይኑ ስርቅ በስሜ ጠራኝ፣ አቤት ሚሩ ና አልኩት የይሉኝታውን ገመድ የመጣይምጣ በሚል በጣጥሼ።  ሁኔታዬን የተረዳው ጋባዤ " ጃንተስር ማይጠፋው ልጅ ነው? ጥራው ከኛጋር ይበላል ብሎ እሱንም ጋበዘልኝ። ሚሩ ድምፄን ወዳሰማሁበት ቦታ ቱርርር ሲል መጣ። በውስጤ ተፈጥሮ የነበረው የሀዘን ስሜት በደስታ ፀዳል በራ። ምሳውን በሚያስደስት መልኩ ተጋብዤ ወጣው፣ሚሩ አብሮኝ በመጋበዙ ሰበብ። እስከዚህ ድረሰ ሆኗል ለሚሩ ያለኝ ፍቅር። ሚሩ፣ ሲስቅ ነብሴ በደስታ ትፍነከነካለች፣ አዝኖ ሲያለቅስ ውስጤ ያነባል። ስሜቱ ከስሜቴ ጋር ከተቆራኘ ቆይቷል። ከጎረቤት ልጅ ጋር ተጣልቶ፣ በልጅ ፀብ ጣልቃ እየገቡ ለልጆቻቸው እያደሉ  እሱን ሲያስከፉት፣ ከልጆቻቸው ጋር እንዳይጫወት ሲከለክሉት፣ እኔ የሰራሁለትን መጫወቻ፣ ሲወስዱበት፣ የኔ ነው  ቢልም ሰሚ ሳያገኝ ሲቀር፣ እናቱም ተጠግታ ከምትሰራበት ሰዎች ላለመጣላት ስትል፣ አርፈህ ቁጭ በል ስትለው፣ ህፃናት ሲጫወቱ እሱ በእናቱ ትዕዛዝ መሰረት ተቀምጦ አኩርፎ ሲጫወቱ ሲመለከታቸው፣ በመሃል ኩርፊያውን ረስቶ ሲስቅ ሳይ ውስጤ በሀዘን ይርዳል። ያሳዝነኛል። ሰው አይመልከተው እንጂ ውስጤ ይጮኻል እንደ ኢያሪኮ ከተማ። ለሱ ያለኝ ስምት ለምን እንዲህ ሊሆን እንደቻለ ምክኒያቱ ግን ሚስጥር ሆኖብኛል። ለሚሩ ያለኝ ፍቅር ተመልካች፣ ወላጅ አባቱ እየመሰልኳቸው፣ ምን አይነት አባት ነው" ብለው አስኪያሙኝ። ድረስ ደርሷል። ወላጅ አባቱ አለመሆኔን ሲያውቁ ምን እንደሚሉ እንጃ።

  ሚሩ በሞባይልህ ጌም አጫውተኝ ሲለኝ። የምጠብቀው አጣዳፊ ስልክ ቢኖር እንኳ፣ ልከለክለው አቅም ያጥረኛል። ማንኛውም ጥያቄ ቢጠይቀኝ፣ የምችለው ከሆነ ለመስጠት ወይም ለማድረግ ለሱ ያለኝ ፍቅር ያስገድደኛል። ሲዘል ሲጫወት በርቀት ሳየው፣ ካሁን አሁን እንዳይወድቅና፣ ክፉ ነገር እንዳይገጥመው በአይኔ የምከላከለው ይመስላል። እንቅፋት ሲመታው ነብሴን ጥዬ ወደሱ ልንደረደር ይከጅለኛል። ከዚህ ቀደም እንኳን ለባዳ ለወንድም እህቶቼ ልጆች እንዲህ እጅ እግር ጠፍሮ በሚይዝ ስጋት ተከታትያቸው አላውቅም። ለዚህም ነው ለሚሩ እንደዚህ መሆኔ ብህይወቴ አዲስ ገጠመኝ የሆነብኝ። ሰው ላልወለደው ልጅ እንደዚህ የሚሆንበት አንጀት እንዴት ይገጥመዋል?

   ቀን እንደዛ አዛ ሲያደርገኝ ውሎ ማታ እናቱ ይዛው ወደ ቤቱ ሲሄድ ሰላም ቻው እሺ ብሎ፣ ደግሞ በጠዋት ና እሺ" እያለ ለስንብት መጥቶ ያቅፈኛል፣ ይስመኛል። ነገ ማላገኘው ይመስል እኔም ደጋግሜ እስመዋለው፣ ናቱ ጋር ተያይዞ  ወጥቶ ይሄዳል። ድምፄ ይከተለዋል፣ "እጇን እንዳትለቅ እሺ፣ መኪና እንዳይገጭህ፣ እለዋለው እሺ ይለኛል ከቀልቡ ባልሆነ መልስ። ስጋት ይጀምረኛል፣ ቀልቃላና እብድ ነገር ስለሆነ መንገድ ላይ መኪና የሚገጨው ይመስለኛ፣ ይህ ስጋቴ መጠኑን አልፎ አንድ ሁለት ቀን በቅዠት  ሲገጭ አይቼ አባንኖኛል። አቦ አልህ ይጠብቀው እንዴት ያለ መከራ ነው እልና፣ ወደ እንቅልፌ ጠልቄያለው።

  በቀን ውስጥ ህፃናት እስከ  500 የሚደርስ ጥያቄ እንደሚጠይቁ ሳይንሱ ያረጋገጠው የህፃን ወግ ነው። የሚገርመው ሚሩ ከአንድሺህ በላይ እየጠየቀኝ ቢውልም እኔ ለመመለስ አልሰለቸውም። የሚጠይቀኝ ጥያቄዎች ደግሞ ከሚገባው በላይ ያስገርመኛል። ለምሳሌ የመኪና ውድድር ጌም ሰጥቸው በሞባይሌ ሲጫውት፣ በጌሙ ውስጥ የሚገጥሙትን እንቅፋቶች፣ አጥፋልኝ ይለኛል አይቻልም ብለው ለምን እንዴት እያለ እንደፍልስፍና ዘርፍ የማያቆም ጥያቄውን ያንቸለችልብኛል። ደግሞ ሲጫወት ላዬ ላይ፣ለመውጣት ሲንጠራራ፣ ሲዘል ፣ፊቴን እየደባበሰ የጥያቄ መአት ሲያወርድብኝ፣ ሳወራ አፍ አፌን በግርምት ሲያየኝ፣ እቅፌ ውስጥ ሆኖ እያወራውለት በድንገት ሌባ ጣቱን አፍንጫዬ ቀዳዳ ውስጥ ከቶ "ትን ሲያስብለኝና ሲስቅ። በደስታ ከመደሰት በቀር መትቸው ይቅርና ተቆጥቸው አላውቅም። አያት እንኳ እንደዚህ አያቀማጥልም። ሚሩ  ነገረ ስራው ሁሉ ያስቀኛል።

  እንዲህ ልሆን የቻልኩበትን ምክኒያት እስከ ዛሬ እንቆቅልሽ ሆኖብኝ ከርሟል። ወይ ሚሩ፣ እንደው ልጅ አልባው አባት ያደርገኝ? ሳልወልደው፣ ከወለዱት በላይ እንድጨነቅለት ያድርገኝ? ይህን ሁኔታዬን ከምን እንደመነጨ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር ስወያይ ነው፣ እንቆቅልሹ የተፈታልኝ። ጓደኛዬ ሚሩን አይቶት "ህፃንነቱ፣ ከዘመኑ ልጆች ለየት ያለ ነው፣ ልብ ብለህ ይህን ልጅ ካስተዋልከው ህፃንነቱ፣ጨዋታው፣ ድርጊቱ የዋህነቱ  በፊት በኛ ጊዜ የነበረውን ህፃንነት አይነት ነው።" አዎ ጓዴ እውነቱን ነው።

  የልጅነት ህይወቱን የሚናፍቅ ሰው እንዳለው ሁሉ፣ ባለፈበት መራራ ገጠመኝ የመጣ ለአፍታ ልጅነቱን ማስታወስ የማይፈልግ ሰው አለ። እምደመታደል ሆኖ እኔ የልጅነት ትዝታቸውን ከሚናፍቁ ወስጥ እመደባለው። ልጅነቴን ማስታወስ ለአስደሳች ትውስታዎቼ ስለሚያንደረድረኝ በጣም እወደዋለው። የሚያስታውሰኝንም ሁኔታና ሰው፣ እያየው በውስጡ የልጅነቴን ትዝታ መከለስ ያስደስተኛል። በተለይ ህፃናትን ማየት። እርግጥ ነው የዛሬ ህፃናት፣ እኔ ባለፍኩበት አይነት የህፃንነት ህይወት በንቃተ ህሊናም ሆነ በብዙ ነገር የተለዩ ናቸው። የልዩነት ምሳሌው መግቢያው ላይ እንደተጠቀሰው።

ሚሩን ልወደው፣ የቻልኩበት ምክኒያት ይህ ነው። አገኘሁት!!   የስድስት አመቱ ሚሩ፣ በኛና በዘመኑ ልጆች ያለውን ልዩነት አጥቦ በመገኘቱ፣ ወደ ልጅነቴ ትውስታ ሸኚ ሳይሆን አድራሼ ስለሆነኝ ነው። እንደ ዘመኑ ልጆች ቆቅ፣ ነገረ ፈጅ፣ ኡላ ነገር አይደለም። ባገኘው ስው ላይ ይንጠላጠላል። የማያውቀውን ሰው ትንሽ ካዋራው ይሄን አድርግልኝ ይላል። የዋህነቱና እንደማውቃቸው እኪዮቹ ሳይሆን ሚሩ የተለየ ነው። አፈር ይበላል፣ ጭቃ እያቦካ ይጫወታል፣ ራቁቱን ሆኖ ሰያብድ፣ሲበጠብጥ ሳየው የራሴ የልጅነት ትውስታዬ በአይኔ ይታየኛል። ልጅነቴን የሚያሳየኝ በዚህ ዘመን ያገኘሁት ሆኖ ተገኝቷል፣ ከሚገባው በላይ እንድወደው፣ ከአባቱ በላይ ለደህንነቱ አሳቢ፣ልጅ አልባ አባት አድርጎኛል። ሚሩ የልጅነቴ መስታወት፣ ሚሩ ሚሪንዳ ግዛ ሲለኝ፣ በልጅነቴ ሚሪንዳ ለመጠጣት የነበረኝ፣በአመት በዓል ቀን የሚሳካው ፍላጎቴ ድቅን ይልብኛል፣ መቆሚያ አልባ ጥያቄዎቹ፣ እኔም በሱ እድሜ እጠይቅ የነበረው ጥያቄና መልስ ትውስ ብሎ ያስቀኛል። እንደውም አንዴ ለአጎቴ ልጅ በልጅነቴ የጠየኩት ጥያቄና የመለሰልኝ መልስ ዛሬም ድረስ ያስቀኛልና መሰነባበቻ ትሆን ዘንድ እነሆ!!
"ኪያር!" አልኩት።
"አቤት"
"አንበሳና ነብር ቢደባደቡ፣ ማን ያሸንፋል?" ብዬ መልሱን በጉጉት ስጠብቅ።
"እኔ አደባድቤያቸው አላውቅም!" ብሎኝ እርፍ።
(ምናለበት አንዱ ያሸንፋል ቢለኝ እስኪ?)።
ወገሬት!!

Thursday, September 8, 2016

"የእሳት ልጅ… "

"የእሳት ልጅ አመድ"
ሳተናው

… ከረጅም አድካሚ የመኪና ጉዞ ቡኋላ ከአቧቷ ቀዬ የሚያደርሰውን ረጅም አውሯ ጎዳና በእግሯ ተያያዘችው። ሸምስ ጉልበቷ ሳይከዳት፣ የልጅነት ዘመኗን የቦረቀችበት፣ ከአቻዎቿ አፈር ቅማ የተጫወተችበት፣ ወጣነት ዘመኗን ያጣጣመችበት፣ በሀይለኝነቷ የተነሳ በአቻ ጓደኞቿ የምትፈራበት፣ በየሰርግ ቤቱ ኮከብ ጨፋሪ ሆና ያሳለፈችበትን ትውስታ ጎዳናውን ስታይ አንድ በአንድ በአይነ ህሊናዋ ተገጠገጠ። አድካሚው ጉዞ ተጠናቆ ከአባቷ ጎጆ ደረሰች። ከረጅም አመታት ቆይታ ቡኋላ ለቀዬዋ በመብቃቷ ደስታውን ለመግለፅ ጎረቤት፣ወዳጅ ዘመድ ሁሉ ተቀበላት። ደስታውን ገለፀላት… አጅቧት ወደ ቤት ይዟት ገባ። የአባቷ ጎጆ ለሷ በሚደረገው ዝግጅትና፣ ሽር ጉድ ልዩ ነበር። ተበልቶ፣ተጠጥቶ፣ ቡና እየጠጣ፣ በደስታ እየተጨዋወተ ነበር። የቤቱ ድባብና ጨዋታ ትኩረት የሚስብ ጉዳይ ቢሆንም። የሸምስን ትኩረት ግን…  ሰዉ እየተሻማ ሲስማት በግርግሩ ከሳመቻት በአንዲት አይነ ትላልቅ ልጅአገረድ ላይ ነበር። የልጅቷም ትኩረት ሸምስ ላይ። በተደጋጋሚ አይን ለአይን እየተጋጫጩ ቆዩ። ሸምስ… የልጅቷን ትላልቅ አይን ባየች ቁጥር ልቧ ድንግጥ ይልባታል። እንደበደለ ሰው በሙሉ አይኗ ማየት ተስኗታል። አይኗን ከልጅቷ ፍፁም መንቀልም አቅቷታል። ቢጨንቃት ቢጠባት…
"ያቺ አይነ ትልልቋ የማን ልጅ ነች?" ስትል አጠገቧ የነበረችውን ሴት ጠየቀች። ሴትየዋም ሁሉን ነገር ስለምታውቅ ሳቀችና "እስኪ በደንብ እያት!"።ሸምስ አንዳች ነገር ግልፅ ባይሆንላትም ጠርጥራለች። ግን እርግጠኛ አልሆነችም።
"እባክሽን አታስጨንቂኝ ማነች?" ገና ሳያት ነው ልቤ ድንግጥ ማለት የጀመረው"። ብላ ለአፍታ ወደ ልጅ አገረዷ ዞረች። የልጅቷ አይኖች አሁንም እሷው ላይ እንደተተከሉ ነበር።
"እንግዲየውስ እርምሽን አውጪ ያንቺው ልጅ ነች"ብላ እንቅጩን ነገረቻት። ሸምስ ይህን ቃል ስትሰማ፣ ሰውነቷ ራደ፣ ቁጭት፣ፀፀት፣ጥፋተኝነት ተረባርበው የልብ ምቷን ያቆሙት መሰላት። ትንፋሽ አጠራት፣ የምታየው ሁሉ ጭልም አለባት። ወደ ነብሷ ስትመለስ አስታወሰች፣አዎ ያቺ! ምስኪን ልጇ፣ የአራስ ቤት ጨቅላ እያለች በእልህ ለአባቷ ጥላት የሄደችዋ፣ የአብራኳ ክፋይ…
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
 
  ከዚህ ቀደም ከሰማዋቸው የእናቶች ታሪክ የአብራኳን ክፋይ በእልህ ጥላ የእንጀራ ልጆቿን በእንክብካቤ ያሳደገች እናት ብትኖር ሸምስ ነች። ሸምሲያ ቡሴር፣ ሳቆላምጠው(ሸምስ)። ለመሆኑ ሸምስ ማን ነች? መልሱን ከአስገራሚው ታሪኳ … ታገኘዋለህ።

   ሸምስ በወጣትነቷ በጣም እልከኛ፣ ሀይለኛ፣ ያሳበችውን ሳታሳካ የማታድር፣ የተሰኘች ብቻ ሳይሆን ሆና የኖረች እንስት ናት ሸምስ። የነዚህ ፀባዮች ባለቤት ብትሆንም በተክለ ቁመናና በመልኳ ደግሞ የተዋበች። አሟልቶ አይሰጥም አንዲሉ። ሀይለኛው ባህሪዋ ከኮረዳነቷ እስከ ብስለቷ ድረስ አብሯት የዘለቀ ቢሆንም፣ እንደ እንከን ተቆጥሮ  ከተፈላጊነት ወይም  ከተወዳጅነት፣ አላገዳትም። እሷን ለትዳር የሚመኝና የሚጠይቀው በርካታ ነው። ለዛ ነው መሰል  ባል ቀያይራ በአራተኛው የፀናችው። ለሶስት ባል ቀይ ካርድ በመስጠት ከእቴጌ መነን  ጋር ምትመሳሰለው ሸምስ መጀመሪያ የተዳረችው ለአንድ ባለ ሀብት ሰው ሁለተኛ ሚስት በመሆን ነበር። አገባች። በትዳር ህይወቷ ቀናት፣ሳምንታት፣ወራት፣ አለፉ። ሸምስ  አ ረገዘች። ሴት ልጅም ወለደች። በአጋጣሚ ሆኖ ጣውንቷም በዛው ሰሞን ነበር ወንድ ልጅ የተገላገለችው። አራሶቹን ለመንከባከብ እንዲመች በሚል ሁለቱም በአንዱ ቤት ተጠቃለው ይታረሱ ጀመር። ሁለት አራስ በአንድ ጊዜ ያስተናገደው ቤት አራስቤት፣አራስ ቤት መሽተቱ አልቀረም። ታዲያ በአንድ ዕለት እንዲህ ሆነ። ሸምስ፣ጣውንቷ ጋር ሁለቱም ህፃኖቻቸውን ታቅፈው ባሉበት፣ ለጥየቃ በመጡ እንግዶች ፊት ባላቸው መጥቶ ቀልድ አዘል ነቆራ ጣል አደረገባቸው። በቀልዱ እንግዳው በሙሉ አስካካ። ሸምስን ቀልዱና፣ሳቁ የንዴት ሞገድ ከእግርጥፍሯ እሰከ ራሷ  ቢያንዘረዝራትም፣ በሰዓቱ ዝም አለች። ጣውንቷ የባሏን ባህሪ ቀደም ብላ በማወቋ ምንም አላለችም። በባሏ ቀልድ ንድድ ያለችው ሸምስ  ምቹ አጋጣሚ ጠብቃ በዛው እለት ገና አጥንቷ ያልጠነከረችው ልጇን ጥላለት ወደ አባቷ ቤት ነጎደች። (ይህን ያህል የአራስ ልጅ አስጥሎ የሚያስኮበልል ምን ቢናገራት ይሆን?) በቃ ልጇን ጥላለት ሄደች። አትንኩኝ ባይነቷና ሀይለኝነቷ የእናትነት አጥር እንኳ አላቆመውም። ድርጊቷ በጊዜው ከነበረው አስተሳሰብና ልማድ ያፈነገጠበት ባል በንዴት ተንጨረጨረ። ጉልበቴን ስማ ትገባታለች ሲል ዛተ። የምትመለስበትን መንገድ በሀይል ሞከረ። አልቻለም። በመጨረሻ  ትመለስ ዘንድ ሽማግሌ ቢልክ፣ አለሆነም።ምን ቢቧጥጥ ወይ ፈንክች ያአባ ቢላዋ ልጅ። ሀይለኛዋ ሸምስ መስሚያዋ ጥጥ ሆነ። ባልም ተስፋውን ቆርጦ ተዋት። የሸምስ ልጅ እንደመንታ የእንጀራ እናቷ ጡት ከወንድሟ ጋር ተጋርታ አየጠባች ማደግ ዕጣ ፈንታዋ ሆነ።

   ሸምስ ሁለተኛ ሚስት ሆኜ  ትዳር አልመሰረትም ስትል ህይወቷ ላይ የምትተገብረው ደንብ አረቀቀች። አግብታ የፈታች መሆኗ ሌላ ባል የማግኘት ዕድሏን አላጠበበውም ነበርና ለሁለተኛ ግዜ ተሞሽራ ተዳረች። ከሁለተኛ ባሏ ጋር ብዙም ሳይቆይ ይኸው ሁለተኛ ባሏ፣ ቅድሚያ ይዛው ከነበረው  አቋሟ የሚፃረር ተግባር ፈፀመ። አልወለደችልኝም በሚል ሰበብ ሳያማክራት እሷ ላይ ሌላ ሚስት አገባ። ሸምስ በንዴት ጦፈች። "ልጅ ስላክወለድኩለት ነው አይደል የደረበብኝ? ቆይ ባልሰራለት ስትል በውስጧ ዛተች። ዝታም አልቀረች። የተደረበችባትን አዲስ ሙሽራ ሀይሎ ጋ ሆ! እያስጨፈረ በዋናው በር ሲገባ። እልኸኛዋ ሸምስ "በል እንግዲህ አልተገናኘንም!" ብላ በጓሮ በር ወደ አባቷ ቀዬ ነካቸው። በቃ! አፍንጫህን ላስ! አለችው። በእልኸኛነቷ ለሁለት ባሎቿ በቢጫ ሳታስጠነቅቅ ቀይ ካርድ አሳይታ ተሰናበተቻቸው። በሁለተኛው ባሏ ሸምሰ በመሄድ ብቻ አልዃ አልበረደም። ከሱ ጋር እሳትና ጭድ የነበረን ሰው አመቻምቻ፣ ለማናደድ ስትል ለሶስተኛ ጊዜ አገባች። ማግባቷ ሳይሆን ጠላቱን ማግባቷ ሁለተኛ ባሏን አሳበደው። ይህን ስታይ የበቀል ጥማቷ ረካ። ያበደው ሆዬ። ሁለቱንም እገድላቸዋለው አለ። ፎከረ ፣ሞከረ፣ በዚሁ የመጣ ሸምስ ከባሏ ጋር ቀዬውን ጥላ ወደ አዲስ አበባ ሸሸች።

  አዲስ አበባን ስትረግጥ ጊዜው በንጉሱ ዘመን መሆኑ ነው። ህይወት በከተማ ተጀመረ። አራት ኪሎ አካባቢ ቤት ተከራዩ። በዛው ቤት ከእለት ጉርስ የማያልፍንግድ ጀመረች። ለስራው አዲስ ስለሆነች ወዲያው ትርፋማ አላደረጋትም ወይንም አላዋጣትም! በዛ ላይ የአራት ኪሎ አካባቢ አብዛኛው ህብረተሰብ ከለመደችው ከኖረችበት ባህል፣ወግ፣ልማድ ሀይማኖት የተለየ በመሆኑ በቀላሉ መላመድ አልቻለችም። አንድ ቀን ለዚሁ ሶስተኛ ባሏ መርካቶ ወንድሞቼ ስላሉ እነሱ ጋር ሄደን ኑሮዋችንን አናሻሽል ሰርተን አራሳችን እንለውጥ ስትል አማከረችው። መልሱ "ሴትዮ አርፈሽ ተቀመጭ  አትንቀዥቀዢ" ነበር። "አርፌ ልቀመጥ? ኧረ! ጣጣህን ቻል!! ብላው ጥላው ወደ መርካቶ። ሸምስ ወንድሞቿ ጋር መርካቶ ገባች። የአይብና ቆጮ ንግድ ጀመረች። (የዛሬው የመርካቶው ቆጮ ተራ ነበር !! አይገርምም።)

እልኸኛዋ ሸምስ ህይወቷን ለብቻዋ ቀጠለች። የሚገርመው ሶስት ባሎቿን ብትፈታም ተተኪ ባል ማግኘት  አልጠጠረባትም። ብዙ ባል እየመጣ እሷን ለትዳር መጠየቅ አልተወም። ያመነችበት ሰላልገጠማት በጄ አላለችም። ከመጀመሪያ ባሏ በተጋባችው እልህ የመጣ የአብራኳን ክፋይ ልጇንን እንኳ ዞር ብላ አላየችም። የእልህኛነቷ ብዛት በአብራኳ ክፋይ እንኳ እንድትጨክን አስገደዳት። በመጨረሻም እዛው መርካቶ ሚስቱ አራት ልጅ አከታትላ ወልዳለት የሞተችበትን ሰው በዘመድ በኩል እንደ አጫት ተነገራት። መልሷ እስኪ ሄጄ አየዋለው ነበር። ጉድ ተመልከት! ሴት ልጅ፣ ወንዱ ቤቷ ሄዶ አይቷትና መርጧት ብቻ በሚያገባበት በዛ ዘመን፣ ሴት ልጅ ማን ያግባት ማን ሳታውቅ ዝም ብላ እንደተመረጠች ተነድታ ወደ ባሏ ቤት መሄድ አግባባዊ ወግ መሆኑ በሚታመንበት በዚያ ዘመን። የሸምስ ድርጊት በተገላቢጦሽ ሆነ።  ያጫትን ሰው ቤቱ ሄዳ አይታው እራሷው እንደሚሆናት እንደማይሆናት ለመወሰን ቀጠሮ አስያዘች። ይህ ድርጊቷ ከአባት ቅድመ አያት ተያይዞ የመጣውን ወግ ልማድ ወደ ጎን ብሎ ተገኘ። የሰማ፣ያየ ሁሉ እንደጉድ መነጋገሪያ ሆነ። በቀጠሮው መሰረት ተደግሶ ወደ አጫት ሰው ቤት ሄደች። ወንድሞቿን እንኳ አስከትላ አልነበረም። ብቻዋን፣ ሄደች ይህ ሁኔታ በራስ የመተማመን መንፈሷ ዘመኑን የተሻገረ መሆኑ ልብ ይሏል። ሰውየን አየቸው! ወዲያው ፎንቃ ጠለፋት! በቃ በአንዴ ወደደችው። እናታቸው ጥላቸው የሞተችውን አራት ህፃን ልጆቹን ስታይ ደግሞ ይብስ ባባች። እሺታዋን እዛው አበሰረች። ድግሱ የተሳካለት ሆነ። በአጭር ጊዜ ውስጥ ለአራተኛ ጊዜ አግባች።እዚህች ጋር  ሸምስን ከሀይለስላሴ ሚስት እቴጌ መነን ጋር የሚያመሳስላት አንድ ጉዳይ ቢኖር በአራተኛ ባሏ መፅናቷ ነው። ስራዋና አቆመች፣ ልጆቹን ማሳደግ ስራዋ አደረገች። ይገርማል!! የራሳን የአብራኳን ክፋይ በእልህ ጥላ የባሏን ልጆች ተንከባክባ በማሳደግ ረገድም የተለየች ያሰኛታል። ፈጣሪ መጀመሪያ ጥላት በመጣችው ልጇ አቄመባት መሰል ጥላት ከሄደችው የመጀመሪያዋ ልጅ ቡሃላ ለሌላ ልጅ አልታደለችም።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
   በሌላው የህይወት ገፅታ ሸምስ አራስ ቤት ጥላት የመጣችው ልጇ ካሳደገቻት ከእንጀራ እናቷ ጋር ተስማምቶ መኖር ቢያቅታት። ቤቱን ለቃ ጠፋች። የአያቷን ቤት በአንድ አጋጣሚ በእንጀራ እናቷ ጋር ሄዳ አይታው ሰለነበር ወደዛው አመራች። መኮብለልን ከእናቷ ሸምስ በዘር የወረሰችው ይመስላል። ቢሆንም የኗቷን ያህል ሀይለኛ አልነበረችም። የእሳት ልጅ አመድ…። አጠያይቃ አጠያይቃ ከአያቷ ጎጆ ደረሰች። በግቢው ውስጥ የነበሩት አያቷ ረጅሙ ጉዞ አድክሟትና፣ አቧሯ በመላ አካሏ ላይ ረብቦ ሲያዩዋት፣ የወላድ አንጀታቸው ተላውሶ አነቡ፣ አለቀሱ። የሸምስ ልጅ  ከዚህ ቡሃላ ኑሮዋ በአያቷ ጎጆ ሆነ። ልጇም አደገች። ሸምስ አባቷ ቤት የምትሄድበት አጋጣሚ ተፈጠረ። ከሸሸቸው ረጅም አመት ወደ ሆናት የትውልድ መንደር ነጎደች …
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••
…   በአባቷ ቤት ከደረሰች ቡሃላ ትኩረቷን ሰርቃ ስታያት የቆየችው ልጅ አገረድ የራሷ ልጅ መሆኗን አጠገቧ ካለችው ሴት ከሰማች ቡሃላ በድንጋጤ የሳተችው አቅሏ ቀስ በቀስ ተመለሰ። አስታወሰች፣ አዎ! ያቺ ያቺ ምስኪኗ ልጇ፣ የአራስ ቤት ጨቅላ እያለች በእልህ ለአባቷ ጥላት የሄደችዋ፣ የአብራኳ ክፋይ፣ እሯሷ መሆኗን አወቀች። ገና ስታያት ልቧ ትር ትር ያለባት፣ በአይኖቿ ውስጥ መበደሏን የሚገልፅ ስሜቷን ደመነብሷ ሹክ ሲላት ኖሯል ለካ። ዛሬ እንደትላንቱ፣ ሀይለኛዋ፣ በእልከኛነቷ ወደር የሌላቷ ሸምስ አይደለችም። እድሜ ገፍቷል፣ አስተውሎቷ በስሏል፣ በወጣትነቷ  መስሎ ያልታያት ጥፋት ዛሬ ታይቷታል። ሸምስ የተሰበሰበው ሰው እያቆራረጠች ተንደረደረች፣ ከመሬት ላይ ስጋ እንደምትሞጨልፍ  ጭልፊት አሞራ ልቅም አድርጋ ልጇን አቀፈቻት። ያገኘችውን አካሏን ሳመቻት። ጥብቅ ባለ እቅፏ ውስጥ አኑራት ረጅም ሰዓት አዬዬዋን አስነካችው። "እኔ ነኝ ገዳይሽ!" ለቅሷዋን የሚያጅብ ተደጋጋሚ ከሳግ ጋር ተቀላቅሎ ከአንደበቷ የሚወጣ ቃል ነበር። በእልከኝነቷ የፈፀመችው ተግባር ጊዜ ልብ ሰጥቶ ፀፀታት። ፀፀቱ የእግር አሳትት ሆኖ መላ አካሏን ለበለባት። ከስህተት እንደመመለስ፣ ጥፋትን አምኖ እንደማስተካከልስ? ምን መልካም ነገር አለ። ይኸው ሸምስ ዛሬ ጥፋቷን አምናለች። ልጇን ከተማ ከኔ ጋር ትኑር ስትል ሸምስ አቧቷን ብትጠይቅም፣ ቤት ውስጥ ሌላ ልጅአገረድ ሰላልነበር የአባቷ መልስ አይሆንም ነበር። ።ሸምስ ልጇን በርቀት የሚያስፈልጋትን ታሟላላት ጀመር። ምንም እንኳ ለልጇ የቁስ ፍላጎቷን ብታሟላም። የእናትነት ፍቅር ሰጥታ አለማሳደጓ የፈጠረባት የስነልቦና ክፍተት ሊሞላላት አልቻለም ነበር። ይህን ክፍተት በምን ልትሞላው  እንደምትችል የዘወትር ሃሳቧ ሆነ። ልጇም ለአቅመ ሄዋን በመድረሷ ተዳረች። ወለደች። ሁለተኛዋን ልጅ በእናቷ ሸምስ ቤት መርካቶ መጥታ ነበር የወለደቻት። በእናቷ ታረሰች። በዚህ ጊዜ በሸምስ ህሊና እንድ ነገር አቃጨለ። ለአንድያ ልጇ የነፈገቻትን የእናትነት ፍቀር፣ ለወለደቻት ልጅ ሰጥታ ልታሳድግ በልጇ ልትክሳት ወጠነች። ልጇን ጠየቀች። ምንም እንኳ ለእናቷ ሸምስ፣ ሙሉ በሙሉ ይቅርታዋን ባትነፍጋትም በዚህ ጉዳይ አድሜ ልክ እንደምትፀፀ ታውቅ ነበረና፣ሳታቅማማ ተስማማች። የሸምስ ውጥኗ ቢሰምርም፣ የልቧን ሊያደርስላት አልቻለም። እናም እንዲህ አለች… "ልጄ!! በህፃንነትሽ የነፈግኩሽን ፍቅር ዛሬ ለልጅሽ በመስጠት ልክስሽ እንደምሻ ጠይቄሽ አላሳፈርሺኝም፣ እንደጨከንኩብሽ አልጨከንሽብኝም… የለቀቅሶ ሳግ ንግግሯን ገታው…  ከዚህ ቡሃላ የምትወልጂውንም ወንድ ልጅ እንደወለድሺው ለኔው ነው የምትሰጪኝ! ቃል ግቢልኝ አለቻት ስሜት በሚሰረስር ድምፅ። ልጇም ቃሏን እንደምትጠብቅ ምላ ተገዝታ ወደ ቀዬዋ ነካችው። ቃል በተጋቡ በሁለት አመቱ ሴት ልጅ ወለደች። እናቷ ሸምስ ቃል ያስገባቻት ወንድ ልጅ ነበር። ድጋሚ በሁለት አመቱ ወለደች። አሁን ወንድ ሆነ። በቃሏ መሰረት አራት ወር ብቻ ከሷ የቆየውን ወንዱን ህፃን ለእናቷ ሸምስ ሰጠች። እስኪጠነክር አብራው ቆየች። ሸምስ ድስታዋ ወደር አጣ፣ ለልጇ የነፈገችውን እንክብካቤና ፍቅር ለልጅ ልጆቿ ያለ ስስት አፈሰሰችላቸው። ይህ ተግባሯ የስነልቦናዋን ክፍተት ቀስ በቀስ ሞላው። በዚህ በእናትና ልጅ የህይወት ታሪክ ሰበብ በአያት ተቀማጥለው ለማደግ የበቁት የሸምስን የልጅ ልጆች አሁን ላስተዋውቅህ? ሴቷ ታላቄ  shtex ስትሆን ወንዱ እኔው ሳteናw ነኝ!! የናቴ ቃል ኪዳን።
ወገሬት!!

Sunday, September 4, 2016

ሸምስ ቡሴር

" ሸ ም ስ      ቡ ሴ ር "
#ሳteናw

   ሸምስ … ከረጅም አድካሚ ጉዞ ቡሃላ አቧቷ ቀዬ ደረሰች። ለሷ አቀባበል ለማድረግ በቅድም አያቴ ጎጆ ቤተሰብ፣ጎረቤት ወዳጅ ዘመድ ሁሉ ተሰብስቦ ለቡና በተቀመጠበት ነበር… የሸምስን ቀልብ አንዲት ህፃን ልጅ የሳበችው። ሸምስ… ህፃኗን ባየች ቁጥር ልቧ ድንግጥ ድንግጥ ትር ትር ይልባት ገባ። ቢጨንቃት ቢጠባት "ያቺ አይነ ትልልቋ ልጅ  ማን ነች? ስትል አጠገቧ የነበረችውን ሴት ጠየቀች"።"ሴትየዋም እስኪ በደንብ እያት!"። አለቻት። ሸምስ አንዳች ነገር ጠረጠረች። ግን እርግጠኛ ስላልሆነች ጥርጣሬዋን ዘላ ወዸ ጥያቄዋ ገባች "እባክሽን አታስጨንቂኝ ማነች?" "እንግዲየውስ እርምሽን አውጪ ያንቺው ልጅ ነች።"……
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••

እስከማውቀው ድረስ በምድር ላይ ከሰማዋቸው የእናቶች ታሪክ የአብራኳን ልጅ በእልህ ጥላ የእንጀራ ልጆቿን በእንክብካቤ ያሳደገች እናት ብትኖር የእናቴ እናት አያቴ ሸምስ ቡሴር ነች።

   አያቴ በወጣትነት ዘመኗ ለምታምንበት አቋሟ ምንም ማንም ሀይል የማይበግራትና በጣም እልከኛ በባህሪዋም ሀይለኛ የተሰኘች ነበረች። ይህ ባህሪዋና እልከኛነቷ ከኮረዳነቷ እስከ ብስለቷ ድረስ አብሯት የዘለቀ ባህሪይ ነበር። በተወረደልኝ የታሪክ መረጃ መሰረት ሀይለኛ ነች!! በሚል ምንም ባል ያላጣች ስትሆን የፈለገችውን ነገር በፈለገችው መልኩ የራሳ የማድረግ ብቃት ከመላበሷ ባሻገር በተክለ ቁመናና በመልኳ የተዋበች ነበረች።   ይህችው ሀይለኛዋ አያቴ ለእናቴ አባት ሁለተኛ ሚስት ሆና ከቤቱ ገባች። እሷና ጣውንቷ በተመሳሳይ ጊዜ ወለዱ፣ አያቴ እናቴን ፣ ጣውንቷ አጎቴን። ሁለት አራስ በአንድ ጊዜ ያስተናገደው የአያቶቼ ቤት አራስ አራስ መሽተቱ አልቀረም። አንድ ዕለት እንዲህ ሆነ። አያቴ ሸምስ በአራስነት ጊዜዋ ከአራስ ጣውንቷ ጋር እየታረሰች ባለችበት ሁኔታ ባሏ መጥቶ ቀልድ አዘል ነቆራ ጣል አደረገባቸው።  ጣውንቷ ምንም አላለችም። አያቴ ግን አፍንጫህን ላስ! አለችውና ገና አጥንቷ ያልጠነከረችው እናቴን ጥላለት ወደ አባቷ ቤት ነጎደች። ታምናለህ በቃ ልጇን ጥላ ሄደች። የእናቴ አባት ትመለስ ዘንድ ሽማግሌ ቢልክ፣ ምን ቢቧጥጥ። ሀይለኛዋ አያቴ መስሚያዋ ጥጥ። እናቴ ከአጎቴ ጋር እንደመንታ የእንጀራ እናቷ ጡት አየጠባች አደገች። አያቴ ሁለተኛ ሁለተኛ ሚስት ሆኜ ባል አላገባም! በሚል አቋሟ ፀንታ በአባቷ ቤት ከሀይለኝነቷ ጋር መኖራን ቀጠለች። ለሁለተኛ ጊዜ ተኩላ ተሞሽራ ተዳረች። ብዙም ሳይቆይ ይኸው ሁለተኛ ባሏ፣ በምታምንበት አቋም የሚፃረር ተግባር ፈፀመ። እሷ ላይ ሌላ ሚስት አገባ። "ልጅ ስላክወለድኩለት ነው አይደል የደረበብኝ ?" ብላእልህ ተናነቃት። በሆዷ ላንተ እልህ የማደርገውን እኔ አውቃለው ብላ ጠበቀች። ሁለተኛው ባሏ አዲሷን ሙሽራ ሀይሎ ጋ ሆ እያስጨፈረ በዋናው በር ሲያገባ። እልኸኛዋ አያቴ "በል እንግዲህ አልተገናኘንም!" ብላ። በጓሮ በር ነካቸው። በቃ! አፍንጫህን ላስ! አለችው። ድጋሚ  ወደ አባቷ ቤትገባች። የባል ገዷ ለሱ እልህ፣ከሱ ጋር ማይስማማ የነበረን ሰው። ለሶስተኛ ጊዜ አገባች። ሁለተኛ ባሏን በሶስስተኛ ባሏ አሳበደችው። እገድላቸዋለው አለ። በዚሁ የመጣ ከዚሁ ባሏ ጋር ለኑሮ  ወደ አዲስ አበባ መጡ።   እንግዲህ ጊዜው በንጉሱ ዘመን መሆኑ ነው። ህይወቷ በአዲስ አበባ ቀጠለች። አራት ኪሎ አካባቢ በነበረው በባሏ ቤት የሻሜታ ንግድ ጀመረች። አላዋጣትም! የአራት ኪሎ አካባቢ ኑሮም አልተመቻትም።(ለፖለቲካ ቅርብ ስፍራ ስለነበር ይሆን?) እንጃ ብቻ አልደላትም። አንድ ቀን ለዚሁ ሶስተኘ ባሏ መርካቶ ወንድሞቼ ስላሉ እነሱ ጋር ሄደን ኑሮዋችንን አናሻሽል ስትል አማከረችው። አይሆንም አላታ። እሷም አፍንጫህን ላሳታ! ብላ። ሶስተኛወንም  ጥላ ወደ መርካቶ ነካቸው። ወንድሞቿ ጋር ገባች። የግሏን ስራ መስራት ጀመረች። አያቴ ሶስት አግብታ ብትፈታም ባል አልጠጠረባትም። ብዙ ባል እየመጣ እሷን ለትዳር መጠየቅ አልተወም። ያመነችበት ሰላልገጠማት በጄ አላለችም። ከመጀመሪያ ባሏ በተጋባችው እልህ የመጣ የአብራኳን ክፋይ ልጇንን እንኳ ዞር ብላ አላየችም። የእልህኛነቷ ብዛት በአብራኳ ክፋይ እንኳ እንድትጨክን አስገደዳት።  በመርካቶ የአይብና የቆጮ ንግድ ጀመረች። (የዛሬው የመርካቶው ቆጮ ተራ በአያቴ ዘመንም ነበር አይገርምም።) እልኸኛዋ አያቴ ህይወቷን ለብቻዋ ቀጠለች። በመጨረሻም እዛው መርካቶ ሚስቱ አራት ልጅ አከታትላ ወልዳለት የሞተችበትን ሰው በዘመድ በኩል እንደ አጫት ተነገራት። መልሷ እስኪ ሄጄ አየዋለው ነበር። ተመልከትልኝ ጉዷን! ሴት ልጅ፣ ወንዱ ቤቷ ሄዶ አይቷትና መርጧት ብቻ በሚያገባበት በዛ ጊዜ፣ ማን ያግባት ማን ሳታውቅ ዝም ብላ እንደተመረጠች ተነድታ ወደ ባሏ ቤት በምትሄድበት ዘመን።  አያቴ በተገላቢጦሽ ያጫትን ሰው ቤቱ ሄዳ አይታው እራሷው እንደሚሆናት ለመወሰን ቀጠሮ አስያዘች። ይህ አድራጎቷ ተያይዞ የመጣውን ወግ ልማድ ወደ ጎን ብላ አዲስ ምዕራፍ ከፈተ (አቦ ጀግና!)። አያቴ ስለሆነች አያሽቃበጥኩላት ወይም እየሞላውህ እንዳይመስልህ የምተረተርልህ ሀቅ ነው። ከፈለክ ድንጋይ ነክሼ እምልልሃለው።( አረ ሲያምርህ ይቅር ከፈለክ አትመን…ህእ)

   በቀጠሮው መሰረት ተደግሶ ወደ አጫት ሰው ቤት ሄደች። አየቸው! ወዲያወ ፎንቃ! በቃ በአንዴ ወደደችው። እናታቸው ጥላቸው የሞተችውን አራት ህፃን ልጆቹን ስታይ ደግሞ ይብስ ባባች። እሺታዋን እዛው አበሰረች። ድግሱ የተሳካለት ሆነ። በአጭር ጊዜ ውስጥ ለአራተኛ ጊዜ አግብታ ህይወትን  ቀጠለች። የራሳን የአብራኳን ክፋይ በእልህ ለባሏ ጥላ የባሏን ልጆች እንደ ልጆቿ በእንክብካቤ አሳደገች።   አያቴ ፈጣሪ መጀመሪያ ጥላት በመጣችው ልጇ አቄመባት መሰል ከእናቴ ቡሃላ ለልጅ አልታደለችም።

  አራስ ቤት ጥላት የመጣችው ልጇ(እናቴ) ከእንጀራ እናቷ ጋር ተስማምቶ መኖር ቢያቅታት። ወደ እናቷ አባት ቤት ጠፍታ መጣች።(በማን ትውጣ?)

   እናቴን ሲያዩዋት በወንድ አያቷ አለቀሱ። እናቴ ከዚህ ቡሃላ  በአያቷ እጅ ህይወቷ ቀጠለች። ከዘመን ቡሃላ አያቴ አባቷ ቤት የምትሄድበት አጋጣሚ ተፈጠረ። የልጇን ወደ አባቷ ቤት መምጣት የማውታቀው አያቴ አባቷ ቤት ገጠር ሄደች። በአባቷ ቤት … ቤተሰብ ሁሉ ተሰብስቦ በተቀመጠበት የአያቴን ቀልብ አንዲት ልጅ ሳበቻት። ባየቻት ቁጥር ልቧ ድንግጥ ድንግጥ ይልባት ገባ።"ያቺ አይነ ትልልቋ ልጅ  ማን ነች?" ስትል አጠገቧ የነበረችውን ሴት ጠየቀች።"ሴትየዋም እስኪ በደንብ እያት!"። አያቴ አንዳች ነገር ጠረጠረች። ግን እረግጠኛ ስላልሆነች ተወችውና።"እባክሽን አታስጨንቂኝ ማነች?" "እንግዲየውስ እርምሽን አውጪ ያንቺው ልጅ ነች።"   አያቴ በተሰበሰበው በሰው መኻል ተንደርድራ ሄዳ ልጇን አቀፈቻት። ረጅም ሰዓት እንዳቀፈቻት። አዬዬዋን አስነካችው። "እኔ ነኝ ገዳይሽ!" "አኔ ነኝ ገዳይሽ!"። ረጅም ሰዓት እናቴን አቅፋ አነባች። ትላንት በጉርምስናዋ የፈፀመችው ተግባር ዛሬ ልብ ስትገዛ ፀፀታት። ፀፀቱ የእግር አሳትት ሆኖ መላ አካሏን ለበለባት። እናቴን ከተማ ወስዳ ለማሳደግ አቧቷን ጠየቀች። ቤት ውስጥ ሌላ ልጅአገረድ ሰላልነበር አባቷም የአባቷም ሚስት በጄ አላሉም።   አያቴ ከዛ ቡሃላ ለእናቴ በርቀት የሚያስፈልጋትን ታሟላላት ጀመር። የቁስ ፍላጎቷን ማሟላቷ፣ የእናትነት ፍቅር ለልጇ አለመስጠቷ የፈጠረባት የስነ ልቦና ክፍተት ሊሞላላት አልቻለም። ዘመን አልፎ ዘመን መጣ። ልጇም (እናቴ) ተዳረች። ወለደች። ሁለተኛዋን ልጅ በእናቷ ቤት መርካቶ መጥታ ነበር  የወለደቻት። ከዚህ ቡሃላ አያቴ እንድ ነገር አሰበች። ለአንድያ ልጇ የነፈገቻትን የእናትነት ፍቀር ለልጅ ልጇ ልትሰጥ። ሲፀፅታት የኖረውን በልጇ ልትክሳት። የልጅ ልጇን ለማሳደግ እዛው መርካቶ አስቀረች። ይህም አያቴን አላረካትም። እናቴ ልጇን እናቷ ዘንድ ትታ ለመሄድ ስትሰናዳ። አስቀምጣ እንዲህ አለቻት። "ልጄ በህፃንነትሽ የነፈግኩሽን ፍቅር ዛሬ ለልችጆሽ በመስጠት ልክስሽ እሻለው። ይህች ልጅ እኔው ጋር ታድጋለች። ከዚህ ቡሃላ የምትወልጂውንም ወንድ ልጅ እንደወለድሺው ለኔው ነው የምትሰጪኝ! ብላ ቃል አስገባቻት። እናቴ ቃሏን እንደምትጠብቅ ምላ ተገዝታ ወደ ቀዬዋ ነካችው። ቃል በተጋቡ በሁለት አመቱ እናቴ ሴት ልጅ ወለደች ይህቺ ልጇ ከሳ ጋር ታድጋለች። እናቷ የገባቸው ቃሏ ወንድ ልጅ ነው። ድጋሚ በሁለት አመቱ ወለደች። አሁን ወንድ ሆነ። በቃሏ መሰረት የአራስነት ጊዜዋን እንደጨረሰች ወንዱን ህፃን ልጇን ለእናቷ ሰጠች። በደንብ እስኪጠነክር አብራው ቆየች። በመሃል ከሱ ተለይቼ መኖር አልቻልኩም ብላ መልሳ ገጠር ወሰደችው። ከተማ ለምዶ ገጠር አልስማማ አለው። ድጋሚ ይዛው ከተማ መጣች። ቀድሞ የነበረው ወዙ የገጠሩ አየር አሟጦት ነበር… በመጨረሻም ለእናቷ ጥላው ሄደች። ህፃኑም በአያቱ ማደጉን ቀጠለ። ህፃኑ ማን እንደሆነ ልንገርህ? እኔው ነኝ። በአያቴ እጅ ማደግ እጣ ፈንታዬ የሆነበትን መንስኤ አሁን የገባህ? ይመስለኛል!!
ወገሬት!!