Friday, May 27, 2016

"የአያቴ ድቤ"

"የአያቴ ድቤ"

#ሳteናw 
  ከቀኑ 9:30 ሲሆን ከት/ቤት ተለቀቅን። ከጓኞቼ ጋር እየተተራረብን በህብረት ግማሽ የአስፓልቱን ጎዳና ሞልተን ወደ ቤታችን እንሄዳለን። ጓደኞቼ በየቅያሳቸው ሲደርሱ አየተሰናበቱኝ እየተተሰናበቱኝ ብቻዬን ቀርቼ ወደቤት ሄድኩ።ግቢ በር ስደርስ ከቤታታችን እየተግተለተለ የሚወጣው የእጣንጭስ የቅቤ ቃና ሲያውደኝ አያቴ ከሰምንታዊ የቡና ስርዓቷ ጋር አተካኖ ማዘጋጀቷን አወኩ…

ስለ ኢትዮጲያ ሲነሳ አብሮ ቡና ይነሳል። ቡናው ሲነሳ ያየነው ያደግንበት ከሌላው አለም የተለየው ከባህላችን አንዱ የሆነው የቡና አፈላል ስነ ስርአታችን ድቅን ይላል። የኢትዮጲያን የቡና ስርአት አያየኸው ብታድግም በድጋሚ ላስታውስህ…

ረከቦት፣ሲኒ፣ምጣድ ወዘተ… ተጣጥቦ ይቀርባል፣ ቡናውን ፍሬውን ከእንክርዳዱ እስኪለይ ይለቀማል … ከሰል ይቀጣጠላል … የተለቀመው ቡና ታጥቦ … በተቀጣጠለው ፍም በጋለው ምጣድ ላይ … ቡናው ይገለጣል … ችሥሥሥ… ብሎ ሲንጫጫ ድምፁ አይደላህም?… ቡናውን እንዳያር በመቁሊያ ይማሰላል (ቡና ጠጣለው ብለህ ሬንጅ እንዳትጠጣ ስትቆላው ጥንቃቄ ያሻል) አጋም ሲመስል በመቁያው ተዝቆ…  ይወጣል … ቡናው እስኪቀዘቅዝ… በጀበና ውሃውን ትጥደዋለህ… ጥፍርህን እንዳትቀረጥፍ ተጠንቀቅና ውቀጠው… እስከዛ ውሃው ፈልቷል… የቡናው ዱቄት በፈላው ውሃ ተጨምሮ በድጋሚ ይጣዳል… ይፈላል… ይወርዳል… ሲሰክን… እየተቀዳ…ከነ ስባቱ አቦሉ ይጠጣል(level one በለው)…ውሃ ተጨምሮ…ድጋሚ ይጣዳል…  ቶናው… ከአቦሉ  ቀጥኖ… ይርሳል… በሰሶስተኛውም… በረካው… ይደርሳል…  እሱም ይጠጣል። ድሮ ነበር ታዲያ ይሄ ሁሉ ማሽሞንሞን!! አሁንማ… ጊዜው እራሱ በረካው ስለተነሳ… አስከ በረካ ብዙም አይጠጣም። በማሽን ተቆልቶ በማሽን ተወቅጦ በማሽን ይፈላል… ቶሞካ በለው!።

  ስለቡና ካነሳው አይቀር… አሳዳጊ አያቴ ታዘወትር የነበረውን የቡና ስርአት አነሳለው። አያቴ ከቡና ጋር ልዩ የሆነ ፎንቃ ነበራት። የአያቴ የቡና አፈላል ስነስርዓት ሶስት አይነት ነበር።
1/ዕለታዊ ቡና፣
2/ሳምንታዊ ቡና፣
3/አመታዊ ቡና በሚል ከፍየዋለው።

☞ ዕለታዊ ቡና:- በየእለቱ ጠዋት፣ቀን፣ማታ የሚፈላው ቡና ነው። ዶክተር እንዳዘዘው መድሃኒት ጊዜው ሳይዛነፍ ይፈላል። የቤታችን የቡና ዕቃዎች በቀን 3 ጊዜ በስራ የመሰማራት ግዴታ ነበረባቸው። ዕለታዊው ቡና ላይ የግቢ ውስጥ ጎረቤት አባም እማም ወራዎች የሚታደሙበት ነው። የቡና ቁርሱ ቤት ያፈራው ማንኛውም ነገር… ዳቦ፣ደረቅ እንጀራ በሚጥሚጣ፣ ንፍሮ ቆሎ ወዘተ… ሊሆን ይችላል። ታዲያ ተማሪ እያለው… ጠዋት ጠዋት  ከእንቅልፌ አላርም ሆኖ  የሚቀሰቅሰኝ… "የኢኮኖሚ ዋልታ
ቡና ቡና… " ከሚለው የሬድዮ ዜማ ቀጥሎ … ቡና ሲወቀጥ የሚወጣው ድም… ድም… የሚለው የወቀጣ ድምፅ ነው።

☞ ሳምንታዊ ቡና:- በሳምንቱ አንድ ቀን ለየት ባለ መልኩ በምሳ ሰዓት የሚፈላ ነው።  የቡና ቁርሱም ቆጮ በአይቤ፣አተካኖ፣3 አዚዝ ወይም በቅቤ፣ በአይብ፣ በሚጥሚጣ የተለወሰ ሩዝ ይሆናል። ጎረቤቶችና ልጆቻቸው ጨምሮ ይታደሙበታል። በዚህ ቀን የቡናው ዝግጅት ገና ከማለዳው ከሰራተኞች አንዷን ወደ መርካቶ ቆጮ ታራ ትላክና አይብና ቡላ ቄጠማ ተገዝቶ ቡላው ተቆልቶ… መጠኑ መለስተኛ ማስታጠቢያ በሚያክል ጣባ ተሰናድቶ… መደብ ላይ ከነበረው የአያቴ አልጋ ስር በትሪ ተከድኖ ይቀመጣል። የምሳ ሰዓቱ ሲደርስ የቡና ዕቃዎች ታጥበው ፀዴ ሆነው ይቀርባሉ። ቄጠማ በሸፈነው የመደቡ ወለል ላይ ሰፊና ትልቁ የስኒ ረከቦት ሲኒዎቹ እንደተገጠገጡበት ከአያቴ ፊት ለፊት ይሰየማል። አያቴ በተመስጦ ቡናውን ትቆላዋለች፣ ታስወቅጠዋለች… ቡናው ፈልቶ እስኪሰክን የግቢ ውስጥ ጎረቤት ይጠራል… (ለነገሩ የዛን ቀን የምግብ ዝግጅቱ ቃና ራሱ ይጠራል)። …በጣባ ተሞልቶ የተሰናዳው ቡላ ይቀርባል… ቡላው ሙሉ በሙሉ በአይብ ይሸፈናል። ከአይቡ በላይ ከሩብ ሊትር ያላነሰ የቀለጠ ቅቤ ይደፋበታል፣ ከዳር እስከዳር ሚጥሚጣ ተነስንሶበት ፣ እጣን ተጫጭሶ … ዱዓ ከተደረገና ካበቃ ቡሃላ… የተቀመመው ቡላ ተለውሶ ለቡና አድምተኛው ይታደላል፣ ያልተገኘው ድርሻው ይቀመጥለታል። የኔ ቢጤዎችም ከዚህ ማዕድ ተቋዳሽ ነበሩ። ታዲያ በዚህ እለት በ9:30 ከትምህርት ቤት ስመጣ… ገና ከጊቢ ቃናው ያወደኝ የቡና ስርአቱ ቢጠናቀቅም… አያቴ ለብቻዋ ተቀምጣ  የመሀመድ አወልን መንዙማ ከፍታ፣ እየቃመች… ቤቱ በእጣንና በቅቤ መዓዛ ታውዶ እደርሳለው። ቲቪ ከፍታለው ብለህ እንዳትጦልበኝ! ብላ ቶሎ ድርሻዬን ታስታቅፈኛለች። አላህ ይርሃማት።

☞አመታዊ ቡና በተለምዶ(የዳዶ ቡና) ይሰኛል። በአመት ሁለት ሶስት ቀን የሚዘጋጅ እናቶች የሚታደሙበት የቡና የዱዓ ስርአት ነው። አስፈላጊና ጊዜያዊ  ፀሎት በሚያሻ ጊዜም በእናቶች ይዘጋጃል… ይህን ስርአት ከሌሎቹ ለየት የሚያደርገው ጎረቤት ሴቶች ብቻ ሳይሆን ሩቅ የሚገኝ ወዳጅ ዘመድ ቀድሞ ተነግሯቸው በእለቱ ስለሚገኙ ነው። በዚህ ስርዓት እናቶቻችን የተመካከሩ ይመስል ነጭ በነጭ ለብሰው ቤታችንን ይሞሏታል… የቡና ስርአቱ በመጠኑ ላቅ ብሎ  እንደ ሳምንታዊው ቡና በቆጮና አይብ ይታጀባል… ከምንጊዜውም በላይ ዱዓው በሁሉም እናቶች በየተራ ስለሚደረግ ዘለግ ያለ ጊዜ ይወስዳል። ቆጮና አይብ በሰሀን ሰሀን ተደርጎ ለደረሰው ሁሉ ይሰጣል። በሰአቱ ላልተገኘ ቆጮው እንደ አነባበሮ በአራት መዓዘን ተጠርዞ አንድ አፍኝ አይብ እየተደረገ ይቀመጥለታል። በመጣ ጊዜ ይገጨዋል።ይህ ስርአት ላይ በእናቶቻችን መንዙማ ይባላል … አያቴ ድቤዋን እየመታች ትቀበላለች፣ መንዙማ ታወጣለች…  ሁሉም እናቶች በየተራ መንዙማ ይላሉ። ዜማቸው ከግቢው አልፎ በሰፈራችን ያስተጋባል።(የአያቴ ድቤ ዛሬ አይጥ ከረታትፎት ጊዜ ጥሎታል… ባየሁት ቁጥር ትዝታ ይጭርብኛል። (አላህ የንአለክ…… አይጥ)

በዚህ የእናቶች ዱዓ ሰበብ የታመመው ይሽራል፣ የጨነቀው ይፈረጃል፣ የታሰረው…ነጃ ፈላህ ይወጣል። … ታዲያ እናቶች ያደረጉት ዱዓ እንዲሁ መሬት የሚቀር ይመስልሃል? አይቀርም

ለምሳሌ የኔን አያቴ የተረከችልኝን እውነተኛ ገጠመኝ ላጫውትህ… ነብስ ሳለውቅ መኮንን ክሊኒክ ተገረዝኩ…  በግርዛቱ በስህተት ይሁን በስፌት ሶስት ቀን ወሃ ሽንት መሽናት ተሳነኝ። አያቴ ጨነቃት ጠበባት… በመጨረሻም የዳዶ ቡና አዘጋጅታ በእናቶች ዱዓ ልታስደርግልኝ ዝግጅት ጀመረች። የተጠሩ አንናቶች በሙሉ ተገኝተዋል። ቡናው ሶስት አዚዙ ቀርቧል እኔን በትንሻ ፍራሼ ላይ በጀርባዬ እንደተኛው ከወገቤ በታች እርቃኔን አድርጋ… ከእናቶቻችን መሀል አጋደመችኝ። በየተራ ዱአ አደረጉልኝ። አላህ ሰማቸው!! ሶስት ቀን ታምቆ የሰነበተው ሽንቴ ሽቅብ ወደ ኮርኒሱ ተነፎለፎለ። ቤታችን በእናቶች እልልታ ተቀወጠች እልሃለው።

አላህዬ ለእናቶቻችን ዱዓ! ፈጣን ምላሽ እንደምትሰጠው የኛንም ዱኣ ስማን! ለዲንህ ብለው የታሰሩ ኡሰታዞቻችንን በዚህ ረመዳን ከቤተሰቦቻቸው ይቀላቀሉ እኛም የህሊና ረፍት እናገኝ ዘንድ ፈጣን ምላሽ ስጠን…  አሚን አትሉምን?

No comments:

Post a Comment