Monday, May 16, 2016

"ህ ል ም"

#ሳteናw

<<ከግልገል ሱሪ(ፓንት) ውጪ እናቴ እደወለደችኝ እርቃኔን እንዴትና? በምን? መልኩ እንደተገኘው በማላውቀው ሁኔታ ዙሪያዬን በከበበኝ ፅልመት ተውጬ በሚያረገርግ አግዳሚ ጣውላ ላይ ተቀምጬ… እራሴን አገኘሁት።

ወደ ዙሪያዬ እየተዟዟርኩ ገላመጥኩ ምንም የሚታየኝ ነገር የለም። የት ነው ያለሁት? እንዴት አዚህ ፅልመት ውስጥ እርቃኔን ልገኝ እንደቻልኩ ምንም የማስታውሰው ነገር የለም። ግራ ተጋብቻለው። የተቀመጥኩበትንና በእጆቼ ዳርና ዳር የያዝኩትን ጠጣር ነገር በመዳሰስ ለማወቅ ሞከርኩ። የተቀመጥኩት ጣውላ ላይ እንደሆነ ተገነዘብኩ በቀኝና በግራ እጄ ዳርና ዳር የተደገፍኩትም በጎኑ የቆመ ጣውላ መሆኑን አወኩ። አሁንም ያለሁበት ቦታ ሚስጥር እንደሆነብኝ ነው። እግሮቼ የረገገጡትንም ወለል ቀኝ እጄን ቁልቁል ሰድጄ በዳበሳ አሰስኩ እሱም እርጥበት አዘል ጣውላ ሆነብኝ። የተሸከመኝ ቁስ መላ አካሉ ጣውላ ከመሆኑ በላይ በቆመበት በዝግታ ያረገርጋል። እንዴ? ምንድነው ነገሩ? የት ነው ያለሁት? ማን ነው እዚህ ያመጣኝ?

እዚህ ከመገኘቴ በፊት ያሳለፍኩትን ጊዜ ለማስታወስ ሞከርኩ ከማንነቴ ውጪ ያሳለፍኩት የህይወት ትውስታ ትዝ ሊለኝ አልቻለም። የተደገፍኩትን በጎኑ የቆመ ጣውላ ሁለቱንም እጆቼ ወደ ፊት አንሸራተትኩ በሄድኩ ቁጥር እየጠበበ ሄዶ አንድ ነጥብ ላይ ሁለቱም እጆቼ ተገናኙ። ምን እንደሆነ መንም ሊገፅልኝ አልቻለም! ግራ መጋባቴ ጨመረ። ባለወኩት ሰበብ በተገኘሁበት አስደንጋጭ እንቆቅልሽ በጣም ፈራሁ!

ሞቼ ተቀብሬ ነው እንዳልል… ተቀምጬ ከተደገፍኩበት  የጣውላ ዘር ውጪ ዙሪያዬ ነፃ ክልል ነው፣ ከፈን የተባለ የጨርቅ ዘርም በዙሪያዬ የለም፣ በየመሃሉም ሽው እያለ ፊቴን የሚዳብሰኝ ስስ አየር… አለ። ወይኔ ጉዴ እሺ የት ነው ያለሁት…?  ኡ… ኡ! ብዬ… መጮህ ቃጣኝ። ደግሞ ያለሁበትን ሳላረጋግጥ መጮሁ ፋይዳው አልታይህ አለኝ። እጅግ ብቸኝነት ተሰማኝ። ይህን ስሜት ከዚህ ቀደም አላውቀውም። የሰው ዘር የተባለ ናፈቀኝ። በዚህ ሚስጥራዊ ብቸኝነት ውስጥ ጠላቴም ቢሆን አጠገቤ ቢሆን ብዬ ተመኘው…!

ቀስ በቀስ አይኔ ከፅልመቱ ጋር ትንሽ ሲላመድ ለውጥ ያሳየኝ መሰለኝ… አንጋጥጬ ተመለከትኩ እንደ አከንባሎ የተከደነብኝን ፅልመተ ሰማይ እዚህም አዚያም ሸንቁረው ብልጭ ድርግም የሚሉ ኮከቦች ታዩኝ። ቀብር ውስጥ እንዳልሆንኩ አረጋገጥኩ። ይህም ትንሽ መረጋጋት ፈጠረልኝ። ከቀብር ውስጥ በማይሻል ሁኔታ መኖሬን ሳውቅ መልሶ ደግሞ ረበሸኝ። መልሼ ለመረጋጋት ሞከርኩ።

አንዳች ድምፅ ሰማው። ትኩረቴን ጆሮዬ ላይ ሰብስቤ ቀሰርኩት … አቅጣጫውን አጤንኩ… የተቀመጥኩበትን ጣውላ ከተሸከመው አረግራጊ ወለል የመጣ ድምፅ ነው። ድምፁ አዲስ አልሆነብኝም። የባህር ወጀብ ስስ ድምፅ ነው። ከዳበስኩት፣ ካየሁት፣ ከሰማሁት አንድ ነገር ብቻ ማወቅ ቻልኩ… የመሬት ዘር የተባለ ደረቅ ምድር በሌለበት በማላውቀው ውቅያኖስ ይሁን ባህር ላይ ተንሳፋ በቆመች ትንሽዬ ጀልባ እርቃኔን መቀመጤን። ይህን ብቻ አወኩ። ወደ እዚህ ከየት እንደመጣው? ለምን እንደቆምኩ? ወዴት እንደምሄድ? አሁንም አላውቅም ወይም ትዝ አላለኝም።

ያለሁበትን ነባራዊ ሁኔታ ባውቅም ቅሉ፣ መነሻና መድረሻዬን አለማወቄ ህሊናዬ እረፍት ነሳው። ግራ ተጋባው። ተስፋ የተባለ ሁሉ በዚህ ብቸኝነት ውስጥ አልታይህ አለኝ። የጀልባው ማረግረግ አንዳች ተስፋ የሚቸረኝ ይመስል… በምኞት አደመጥኩት። ከመወዝወዝ ውጪ መልስ የለውም። አይኔን ወደ ሰማዩ አንጋጥጬ ቀረው… አተኮርኩበት… ያተኮርኩበት የሰማይ ግድግዳ ላይ ሴኮንዱና ደቂቃዎቹ የሚዘውሩ ሰዓት
ከየት መጣ ሳልለው ገጭ ብሎ መቁጠር ጀመረ። ተስፋዬን ወደ ሰዓቱ አዞርኩ። የደቂቃው መዘውር ሙሉ ሰአት ላይ ሲደርስ አዲስ ነገር ሊፈጠር ይችላል በሚል ተስፋ። የመጨረሻዎቹ 5 ሴኮንዶች ላይ ደረስኩ… የልብ ምቴ ይሰማኝ ጀመረ … 55… ድው ደው… 56… ድው ደው… 57…ልቤ ይደልቃል…
58… ድው ደው… 59… ድው ደው… 00…

ልክ በዚህ ቅፅበት ይህ ሁሉ ተከሰተ…
አይኔ አይቶት የማያውቀው ብርሃን በዙሪያዬ ፈነጠቀ። እንዴት እንደሆነ ባላወኩት መልኩ ከወተት የነፃ ልብስ ተጎናፀፍኩ… ጀልባዬን የተሸከማት አረግራጊው የውሃ ሜዳ… ቁልቁል… ወደ ሚንዥቀዥቅ ፏፏቴ ተለውጦ… ከጀልባዬ ጋር ይዞኝ ቁልቁል ከነፈ። ከቀኝና ከግራዬ ልዩ ልዩ የፍራፍሬ ተክሎች ከውሃው ውስጥ ብቅ ብቅ ይሉ ጀመር… በድንጋጤ ይሁን በደስታ… ሱብሃን አላህ!! ብዬ ጮህኩ። አንደበቴን ጥሶ የወጣው ድምፄ ከእንቅልፌ አባነነኝ።>>ብሎ ዛሬ ጓደኛዬ ያየውን ህልም ነገረኝ።
ህልሙ ቅዠት ይሁን ምን እስካሁን ፍቺው አልተገኘም።
••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••••√
<<ሞቼ ተቀብሬ ነው እንዳልል… ተቀምጬ ከተደገፍኩበት  የጣውላ ዘር ውጪ ዙሪያዬ ነፃ ክልል ነው፣ ከፈን የተባለ የጨርቅ ዘርም በዙሪያዬ የለም፣ በየመሃሉም ሽው እያለ ፊቴን የሚዳብሰኝ ስስ አየር… አለ።>>

1 comment: