Monday, May 30, 2016

Anwar abdo yahya

Anwar abdo yahya
#ሳteናw
ስታዲየም ፊት ለፊት ከሚገኘው ላሊበላ ሆቴል እንድንገናኝ ቀጠሩኝ… አንዋርና፣የእህቱ ልጅ አዚዝ። በቀጠሮው መሰረት ልብሶቼን በትንሽዬ ቦርሳ አንጠልጥዬ፣ ካሉኝ ቦታ ቀድሜ ደረስኩ። ከሆቴሉ ገብቼ ውጪውን ከሚያሳይ ስፍራ ተቀምጬ ያዘዘኩትን ሚሪንዳ አየተጎነጨው፣ ጎዳናው ላይ አላፊ አግዳሚውን እያየው ቆየሁ። አንዋርና አዚዝ አፍታም ሳይቆዩ በጊዜው ለከተማችን የመጀመሪያ የሆነችውን ቶዮታ ያሪስ አውቶሞቢል ይዘው ከች አሉ። አዉቶሞቢሏ በአንዋር አማካኝነት ከቀረጥ ነፃ ወደ ሀገር ከገባች ገና አስር ቀን እንኳ አልሆናትም። ከአዲስነቷ ጋር አዲስ ሞዴል ስለነበረች ባለፈችበት ጎዳና ሁሉ የሰውን አይን ብቻ ሳይሆን ቀልብም ትስባለች። ከራስ ሆቴል ሂሳቤን ከፍዬ ወጥቼ ወደ መኪናዋ ገባው። አብረውን የሚሄዱ ዘመዱ ሚልዮንና… ችኳንታውን ካሉበት ፒክ አድርገን ጉዞአችንን ጀመርነው …  ወደ ሶደሬ… ዋቢ ሸበሌ ሆቴል…

  ቀጥሎ የምነግርህ ስለ አንድ ታዋቂ እግር ኳስ ተጫዋች ወይም ታዋቂ ስለሆነ ሞዴል አይደለም። ይልቁንስ በጣም የምወደውና የማከብረው አብሮ አደግ ወንድሜ ስለሆነው አንዋር አብዶና ለሽኝቱ ስላሳለፍነው የሶደሬ ጉዞ ገረፍ ገረፍ ትውስታዎች እንጂ። ላንተ በጣም አሳሳቢ ጉዳይ ስላልሆነ ብታነበውም! ባታነበውም፣ ለውጥ የለውም። ምናልባት አስቂኝ ገጠመኞች ስለተካተቱበት ፈገግ ሊያሰኝህ ይችላል…

   አንዋር አብዶ ያህያ፣  ከልጅነቱ ጀምሮ ዕድል የምትከተለው ቅንነት መለያው የሆነ በአንድ ግቢ አብሮኝ ያደገ ልጅ ነው(ታላቅ ወንድሜ ነው ልበልህ አንጂ)። የየመን ዝርያ ስለነበረው፣ ገፅታው የአረብ ፀጉሩ የህንድ፣ የመሰለ፣ ውበት ያፈሰሰበት… የቷንም ሴት "ውይ ሲያምር" የሚያስብል መልከመልካምነት ተፈጥሮ የተቸረ ነው ስልህ ከምሬ ነው። ታዲያ በፊት ከመልኩ ጋር በተያያዘ ማስታውሰው…  ፒያሳ ለፒያሳ ወክ ስናደርግም አላፊ አግዳሚ ቆንጆ ሴቶች አይኑን ሊያወጡት ይደርሱ ነበር። የዚህኔ እኔ በቅናት ይሁን በቅንነት በግልምጫ አፈር ከድሜ አግጣቸውለው።  "ምኗ ደረቅ ነች! ልትበዪው ነው እንዴ!" አላታለው። እሱ አፌን በመዳፉ ለመሸፈን እየታገለኝ  ይስቃል… ተወደድኩ ብሎ ማይመፃደቅ፣ ኩራት የሚባል ነገር ጨርሶ የማይነካካው… ምርጥ ልጅ ነው አንዋር። እኔ የሱ አይነት ገፅታና ስብዕና ቢኖረኝ ኖሮ ስንቷን… ሆ! ሞቼልህ  ዛሬ ይህን ታሪክ ለመፃፍ አልበቃም ነበር kkk  ሌላው ደግሞ አለባበሱ። ብታምንም ባታምንም ለመጀመሪያ ጊዜ ባለ1000 ብር ማጫ ያየሁት አንዋር እግር ላይ ነበር። ታዲያ ምን ያስገርማል? እንዳትል! ይሄ የዚህ ዘመን ሳይሆን የ80ዎቹ መጨረሻ ወሬ ነው። ዛሬ ሀይሉ ሻውል ሞል ባለ 40000 ብር ጫማ መሸጡ ስትሰማ እንደሚገርምህ ሁሉ  በጠቀስኩልህ ጊዜ የ1000ብር ጫማ አስገራሚ ዋጋ ነበር። አንዋር መልክና አለባበስ ብቻ አይደለም… ብዙ መልካም የምትላቸው ስዕብናዎች ባለቤት ነው። ለምሳሌ ባህሪው የተቸገረ ሰው አይቶ ማለፍ ፣አይችልም። "ሰላም ና! ለአከሌ ይሄን ብር እኔ እንደሰጠሁት ሳትነግረው ስጠው" ብሎ  ይልከኛል። ዛሬ ሰው አንድ ውለታ ቢውል በቱልቱላና፣በነጋሪት ላላፊ አግዳሚው እዩልኝ ስሙልኝ መከራ ነው። የእርዳታ ድርጅቶችም አንድ እጃቸው ረድተው በአንድ እጃቸው ቪዲዮ ይቀርፁሃል። አየኸው አንዋር  ሲሰጥ እንኳ በሚስጥር ነው። (ይህ ተግባሩ ሁሌም እንዳከብረውና እንድወደው የሚያስገድደኝ ነው)። በዚህም ሰበብ አንድ ቀን በገንዘብ በኩል ተቸግሮ አያውቅም። ተማሪ እያለም እንኳን።

… ስማ የአዲስ ከቴ ተማሪ ችኳንታዎች… በሱ የመጣ ሚኒ ሚዲያ ያጣብቡ እንደነበር ብነግርህስ…   ከጃሊያ ወጥቶ አዲከተማ ሃይስኩል በሚማር ግዜ ዩኒፎርም አልተጀመረም ነበርና… በዘመኑ ድንቅ የነበረ የአለባበስ ስታይል የሚከተል፣ሁሌ ንፁህ፣ዛሬ የለበሰውን ነገ የማይደግም፣ በዘመናችን ቋንቋ ፀዴ ልጅ…  ታዲያ ይህ ፅዱነቱ፣ በዛላይ መልከ መልካምነቱ የማረካቸው የአዲስ ከተማ ሀይስኩል ኮረዳ ተማሪዎች፣ ለአንዋር ሙዚቃ ለመምረጥ የትምህርት ቤቱን የሚኒ ሚዲያ ቢሮ በሰልፍ ያጨናንቁት ነበር። 15 ደቂቃው የእረፍት ጊዜ አየር ሰዓት ለሱ በተመረጡ ዜማዎች ይጠናቀቁ ነበር። ወደው መሰለህ? ከመልኩ ጋር ያለው መልካም ስነምግባር ያዩት ሁሉ የቀረቡት ሁሉ እንዲመኙት ያስገድድ ነበር።   ምነው አውቀኸው ባህሪውን ብትረዳው… ነጠላ ዘፈን ትለቅነት ነበር።
ከኔ ጋር የነበረን ቅርርብነት እንደማንኛውም የጎረቤት ልጅ ሳይሆን እንደታላቅና ታናሽ ታላቅ፣ እንደልብ ጓደኛ አይነት ነበር። አኔ እንኳ አንድ ነገር አድርግልኝ ካልኩት፣ ያለምንም ጥርጥር አድርጎታል። ከሱ ጋር በነበረን ቆይታ የገጠመኝን ልንገርህ…

  አንድ ቀን ፒያሳ ከሚገኘው እውቁ ገብረትንሳይ ባቅላቫ ቤት  ሄድን፣ አንድ አንድ አዘን በቁም መብላት ጀመርን። አንዋር ሶስቴ እንደጎረሰ ዘጋውና አቆመው እኔ አስገባዋለው። በጊዜው ተማሪ ስለነበርኩ የገንዘብ እንጂ የሀፒታየት ችግር አልነበረብኝም፣ የራሴን እንዳጠናቀቅኩ ወደ አንዋር ባቅላቫ ዞርኩ ፣አቀርቅሬ እጠበጥበዋለው…  ለተመልካች ሰዓት ሰሪ እመስል ነበር፣ ለካ አንዷ ኮበሌ በአበላሌ ተመስጣ ኖሮ ቀና እስክል ትጠብቀኛለች። አድናቂህ ነኝ ፈርምልኝ ልትለኝ አልነበረም። ቀና ስል አይን ለአይን ተጋጨን… በምልክት ና! የኔንም ጨርስልኝ አትልም!…  ንድድ አለኛ…  ሁኔታችንን ሲከታተል የነበረው አንዋር መርካቶ እስኪደርስ ሳቁን ማቆም አልቻለም። እኔም በንዴት እንደዚህ አይነት ሰርጎ ገብ ቡዳዎች እያሉ በየት በኩል እንብላ እልኩት!  የልጅቷ ድፍረት ቢያናደኝም ለአንዋር የሳቅ ምንጭ ስለነበረች ምንም የመልስ ምት ሳልሰጣት ተውኳት።

  አንዋር አዲስ ከተማ ሁለተኛ ደረጃ 12ኛ ክፍልን ካጠናቀቀ ቡሃላ፣ ማይክሮሊንክ ኮሌጅ በኢፎርሜሽን ቴክኖ ዲኘሎማውን ወስዶ ወደ ህንድ በመሄድ የትምህርት ደረጃውን አሳድጎታል። የአንዋርን ስብዕና ብተነትነው ብተነትነው ማሰልቸት ስለሆነ ላቁመው። እድል የሚከተለው ልጅ ነበር ብዬህ አልነበር?  በአንድ ቀን ተደጋጋሚ ብስራት ስለደረሰው ገጠመኝ ላጫወትህ… 

  ትዝ ይለኛል በዚህ ቀን እኔና ጓደኛዬ ሄኖክ አትክልት ተራ ሽንኩርት በኪሎ ለመግዛት በዛውም ፓስታ ቤት የመጣ ደብዳቤ ካለ ለመጎብኘት ወደ ፒያሳ ሄድን… እኔ ሽንኩርቴን ገዝቼ ለጃሬ ሂሳብ እያመቻቸው ወደ ፖስታ ቤቱ ገባን። ሄኖኬ የፓስታ ሳጥኗን ከፈታት ከአንድ ብጣሽ ወረቀት በቀር አላገኘንም። ወረቀቷ አንዋር አብዶ ዲቪ ስለደረሰህ የተላከልህን ፎርም ቀርበህ ውሰድ የሚል ወረቀት ነበር። ጓደኛዬ ሄኖክ በደስታ ጩኸ። እኔ ሀሳቤ ጃሬ ላይ ስለነበር በወቅቱ ደስታዬን አልገለፅኩም። ልክ ሰፈር ስንደርስ ሽንኩርቱን ቤት አድርሼ …  ወረቀቷን ይዘን እነ አንዋር ቤት ገባን…  ብስራቱን ለቤተሰቦቹ ነግረናቸው እየተደሰትን ሳለ በዛው ቅፅበት አንዋር ከህንድ ደወለ …(አይገርምህም አጋጣሚው) አንዋር በትምህርቱ በከፍተኛ ነጥብ ማለፉን ለቤተሰብ ለማበሰር ነበር አደዋወሉ። ለብስራት ደውሎ ብስራት ተነገረው ደስታው ወደር አጣ። ከጥቂት ወራት ቡሃላ አን ዋር ግራጁዌሽኑን አጠናቆ አዲስ አበባ ገባ። የዲቪው ኘሮሰስ በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጠናቀቀ። ቪዛው በእጁ ገባ። ይህን ተከትሎ የደስደስ ወደ ሶደሬ… ለመዝናናት ራስ ሆቴል ተገናኝተን ጉዞውን ጀመርን…

…ደስ የሚለውን የአዲስ አበባ አየር ሰንጥቀን ቁልቁል ተምዘገዘግን ቃሊቲ፣ገላን፣ዱከም፣ እድሜ ለያሪሷ ፉት አልናቸው ደብረዘይት፣ሀይላንድ ውሃ  ለመግዛት፣ቆምን ሄድን… ደግሞ ለሽንት፣ ለፎቶ ምናምን ቆምን…  ደግሞ የሞጆን አውራ ጉዳና… አልፈን  ወደ ናዝሬት።

በረሃ ላይ የተመሰረተች የምትመስለው ናዝሬት (አዳማ) ከተማ 10:00 ሰአት ላይ ደረስን። በመኪናዋ ሰበብ የአብዛኛውን የከተማዋን ሰው አይን ተቆጣጠርነው ብልህ እትት እንዳይመስልህ የምሬን ነው። እዛው ካለ መንዲ ቤት ምሳ በልተን ወደ ሶደሬ ነካነው…  ገባን። አርብ ከቀትር ቡሃላ ስለነበር ግቢው ውስጥ እንደኛው ለመዝናናት በመጡ ሰዎች ተሞልቷል። እንደ ደረስን ቀድመን አዲስ አበባ ዋቢሸበሌ የያዝነውን ሁለት አልጋ ያሉት ሁለት ክፍል ተረከብን። ከክፍሉ ውጪ የሚታዩት ዛፎች፣አዕዋፋት፣ ጦጣዎች ነፋሻማው አየር ተደማምረው የሚሰጡህ ድባብ የነብስ ምግብ ነው ብልህ ማጋነን አይሆንም። ከሻወርና ከእረፍት ቡሃላ ቁምጣ ለብሰን ፎጣ ይዘን ወደ አባድር ፍል ውሃ ገንዳ ሄድን።

በአባድር የመታጠቢያ ገንዳ ገና ስትገባ የምታየው የቦርጭ መዓት የሀገሪቱ ሀብት በገላቸው ላይ በተሸከሙ ባለ ጊዜዎች እንደተከበብክ ይገባሃል።
የአባድር ፍል ውሃ በወፍራሙ እየተምዘገዘገ ቁልቁል ሲንዠቀዠቅባቸው ሳይ ወንድሜ  እኔ በየትኛው አቅሜ እቋቋመዋለው ብዬ ፈራው። ደግሞ ይህ እድል ድጋሚ በህይወቴ ላይገጥመኝ ይችላል ብዬ በወላፈናማው ውሃ ውርጂብኝ ውስጥ ለመግባት ወሰንኩ። ሰውነቴን የውሃውን ወላፈኑን ሳልለማምድ ዘው ብዬ ገባው። ወይኔ ጉድ ሆንኩልህ!! የውሃውን ቃጠሎ መቋቋም አቅቶኝ ድምፅ ሳላሰማ ዘልዬ እንደገባው ዘልዬ ወጣው። አይኔን ሳልከፍት ህመሜን ዋጥኩት። እግሬ በተረበበ ነገር የተሸፈነ መሰለኝ። ውሃው የጀርባ ቆዳዬን ገሽልጦ ከእግሬ የሞጀረው መስሎኝ ደንግጬ ቀስ ብዬ አይኔን ገለጥኩት። ለካ እግሬን የሸፈነው በውሃው ግፊት የወለቀው ቁምጣዬ ነበር። ቀና ስል ሰው እየሳቀ ስስ ጉተና የበቀለበት ሙርጤን ይመለከተዋል። የአንዋርና የአዚዝ ሳቅማ መርካቶ ድረስ የሚሰማ እስኪመስል ነበር…ካካካካ  እንኳን ይችን አግኝቶ… !! የማንንም ሳቅ  ከምንም አልቆጠርኩት። እንትኔ ከቁምጣው ጋር አብሮ ባለመውለቁ ፈጣሪዬን እያመሰገንኩ መልሼ ቁንጣዬን አጠለኩት።በሶደሬ መዝናኛ… ሶስት ቀን በፈረስ ግልቢያ፣ በዋና… መዝናኛ በተባለ ሁሉ አሳለፍን… የማይረሳ ደማቅ ትውስታ ፈጥረን ተመለስን። የሶደሬው የአዋሳው የወንዶ ገነቱ በሌላ ፅሁፍ ዘርዝሬ እቸከችከው ይሆናል።አሁንግን በቃኝ።

አንዋር ዛሬ ስቴት ውስጥ አግብቶና ወልዶ ይኖራል፣ ባለበት ሁሉ ሰላሙን፣ እመኝለታለው።
ወገሬት!!

No comments:

Post a Comment